1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የምሥራቅ አፍሪቃ ወጣት ትውልድ እና እጣ ፈንታው

ሐሙስ፣ ሐምሌ 6 2009

የምሥራቅ አፍሪቃ ሕዝብ በዓመት በ3% እያደገ ነው። እአአ 2100 በአፍሪቃ አራት ቢልዮን ሰው እንደሚኖር ግምቶች ያሳያሉ። ዓ/አቀፉ የገንዘብ መርህ ድርጅት እንደሚለው፣ በቂ የስራ ቦታ፣ ምግብና ማህበራዊ አገልግሎት እስካለ ድረስ ወጣቱ ፈጣን የኤኮኖሚ እድገት ለማስገኘት ጥሩ እድል ይፈጥራል። ይሁንና፣ የስራ ቦታን በተመለከተ ትልቅ ችግር ይታያል።

https://p.dw.com/p/2gUTn
Symbolbild Arbeitslosigkeit in Afrika
ምስል picture-alliance/dpa

mmt Problem oder Chance Ostafrikas schnell wachsende jugendliche Bevölkerung - MP3-Stereo

የእጅ ስልክ ቁጥሯ እና በምጣኔ ሀብት ትምህርት የተመረቀችበት የዩኒቨርሲቲ ዲፕሎማዋ የሚታይበት ሰሌዳ ይዛ በናይሮቢ የሊሙሩ ጎዳና የምትዘዋወረዋ  ወጣት  ራኪየል ካኦካ የስራ ፍለጋ ጥረቷ ተሞክሮ አበረታቺ አለመሆኑን ትናገራለች።
« ከ500 ለሚበልጡ የስራ ቦታዎች ለማመልከት ሞክሬ ነበር። »
 ሆኖም፣ የስራ ፍለጋ ጥረቷ ሳይሳካ ነው እንደቀረ የዶይቸ ቬለ ዘጋቢ ሊንዳ ሽታውደ ገልጻለች። በአፍሪቃ ልክ እንደ ራኪየል ከ14 እስከ 24 ዓመት የሆናቸው ወደ 200 ሚልዮን የሚጠጉ ወጣቶች ይኖራሉ። ይኸው ቁጥር እስከ ጎርጎሪዮሳዊው 2050ዓም በእጥፍ እንደሚጨምር ይጠበቃል። በዓለም አቀፉ የገንዘብ መርህ ድርጅት፣ በምህጻሩ «አይኤምኤፍ»የአፍሪቃ ምክትል ዳይሬክተር ሮጀር ኖርድ አስተያየት፣ ይህን ያህል ግዙፍ ወጣት ሰራተኛ ኃይል መኖሩ ለአህጉሩ ትልቅ እድል ነው ይላሉ፣ ግን ይህ እውን ይሆን ዘንድ፣ የተወሰኑ ቅድመ ግዴታዎች መሟላት ይኖርባቸዋል። 
 « ትክክለኞቹ የኤኮኖሚ እና ማህበራዊ ፖሊሲዎች ስራ ላይ ከዋሉ፣  በ2050 ዓም  ከሰሃራ በስተደቡብ የሚገኘው አፍሪቃ ጠቅላላ ብሔራዊ ገቢ ፣ ካለ ሕዝብ ቁጥር ጭማሪ ይመዘገባል ተብሎ ከሚጠበቀው ፣ በ50 ከመቶ ከፍ ሊል ይችላል ማለት ነው። »
ችግሩ ግን እንደ የደቡብ አፍሪቃ የወጣት ስራ አስኪያጆች ማህበር አባል ማቡቶ ምቴምቡ እነዚህ ትክክለኛ የኤኮኖሚ እና ማህበራዊ ፖሊሲዎች ተጓድለው መገኘታቸው ነው። 
« በሕዝብ ቁጥር ላይ ይታያል የሚባለው ጭማሪ  ለአህጉሩ እምቅ ሀብት እንዲሆን  እንመኛለን። ይሁንና፣ አሁን እንደሚታየው ፣  በማንኛውም ጊዜ ሊፈነዳ የሚችል አስጊ ሁኔታ ላይ ነው የምንገኘው። ምክንያቱ ደግሞ ወጣቶቹ ተርበዋል፣ አልተማሩም፣ ስራ አጥም ናቸው።
አንዱ የሆነው ዴቪድ ንጌቺ ከሰል አምርቶ መሸጥ ተገዷል። አንዱን ኬሻ ከሰል 500 ሽሊንግ፣ ብሎም፣ ወደ አምስት ዩሮ ገደማ ይሸጠዋል።
« መሸጥ እስክችል ድረስ አንድ ወር መጠበቅ አለብኝ። ምናልባት ከዚያ በወር በአማካይ አምስት ኬሻ ብሸጥ 2,500 ሽሊንግ አገኛለሁ። » 
25 ዩሮ እንኳን አይሞላም። እርግጥ ይህ ገቢ ለመኖር ያህል ቢበቃም፣ ለአንድ ከዩኒቨርሲቲ  በምጣኔ ሀብት ትምህርት በዲፕሎማ ለተመረቀ ሰው  እጅግ አነስተኛ ነው። ኬንያ ውስጥ የከፍተኛ ትምህርት ዋጋ በጣም ውድ በመሆኑ፣ የዴቪድ እናት የልጃቸውን ትምህርት ወጪ ለመሸፈን ብዙ መስራት ነበረባቸው። 
የኬንያ ኤኮኖሚ ባለፉት ዓመታት በተከታታይ ስድስት ከመቶ እድገት አስመዝግቧል። ሀገሪቱ በምሥራቅ አፍሪቃ ጠንካራዋ ኤኮኖሚ ብትሆንም፣ ከፍተኛው የስራ አጥ መጠን፣ የሚታይባት ሀገር ናት፣ የስራ አጡ መጠን በወቅቱ 20 ከመቶ ነው።
ይህን ችግር ለማቃለል ወጣቶችን  ለስራ ዓለም ዝግጁ ሊያደርጉ እንደሚገባ የአንድ ስራ አማካሪ ድርጅት ባልደረባ ሮቢ ማቲንዪ ገልጸዋል።
« ለዚህም ትምህርት እና የሙያ ስልጠና የግድ ያስፈልጋል። ወጣቶቹ ቧንቧ ሰሪነት፣ የኤሌክትሪክ ሰራተኛነት ወይም መሰል ሙያዎችን የሚማሩባቸው የስልጠና ማዕከላት መከፈት ይኖርባቸዋል። ራሳቸውን ለስራ ዝግጁ እንዲያደርጉ በነዚህ ዓይነቶቹ ሙያዎች ማሰልጠን አስፈላጊ ይሆናል። »
የስራ ቦታዎችን ለመፍጠር የመሰረተ ልማቱ ግንባታ መስፋፋት ለስራ ቦታ ፈጠራ ተልቅ ሚና ይይዛል። ኬንያ በዚህ ረገድ ልክ እንደሌሎቹ ሀገራት ብዙ እየሰራች መሆኗን ሮቢ ማቲንዪ ቢገልጹም፣ ይህ ከሀገሪቱ ሕዝብ ቁጥር እድገት ጋር ተመጣጣኝ አይደለም። 
« በያመቱ 11 ሚልዮን ወጣቶች ስራ ይፈልጋሉ፣ የስራ ገበያው ግን ሊቀበለው የሚችለው ሶስት ሚልዮኑን ብቻ ነው። እርግጥ፣ ይህን ጥያቄ ለመመለስ አንዳንድ ስራ እየሰራን ነው፣ ግን፣ ፍጥነታችንን መጨመር ያለብን ይመስለኛል። »
የአፍሪቃ ወጣቶች ለአህጉሩ ብሩህ የወደፊት እድል ያስገኛሉ ተብለው ከታሰቡ፣ ይላሉ ማቲንዪ፣ እነሱም ራሳቸው ብሩህ የወደፊት እጣ የሚያገኙበት እድል ሊመቻችላቸው ይገባል።

Afrika Computer Schüler aus Johannesburg 2013
ምስል Alexander Joe/AFP/Getty Images
Jugendliche in Monrovia
ምስል DW

አርያም ተክሌ

ሸዋዬ ለገሠ