ኮሎኔል መንግስቱ እና ፍትህ
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 5 2010ኤሜርሶን ማናንጋግዋ አዲሱ መሪ ሆነው ስልጣን መያዛቸው በዚምባብዌ ዜጎች ብቻ ሳይሆን በሌሎች አፍሪቃውያንም ዘንድ ብሩሕ ተስፋ አሳድሯል።ምናንጋግዋ የኤኮኖሚዉንና ማህበራዊ ችግር እንደሚያበቁና ወንጀለኞችንም ወደ ፍትህ እንደሚያቀርቡ ቃል መግባታቸው ይታወሳል።
ከ26 ዓመት በፊት የቀድሞዉ የዝምባቡዌ ፕሪስዳንት ሮቤርት ሙጋቤ ለኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም የፖለቲካ ተገን መስጠታቸዉ ይታወሳል። የአምነስት ኢንቴርናሽናል ዘገባ እንደሚጠቁመው፣ ኮሎኔል መንግስቱ 17 ዓመት ስልጣን በቆዩበት ወቅት በተለይም በቀይ ሽብር ዘመን ወደ ግማሽ ሚሊዮን ሰዎች ተገድለዋል። እንደ ጎርጎረሳዊያኑ በ2006 ዓ/ም የኢትዮጵያ ከፍተኛ ፍርድቤት ኮሎኔል መንግስቱ በሌሉበት የሞት ቅጣት በይኖባቸዋል። በዚያን ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስት ዝምባቡዌ ኮሎኔል መንግስቱን ወደ አገራቸዉ እንድትመልስ ቢጠይቅም ኮሎኔል መንግስቱ በዝምባቡዌ የነፃነት ትግል ላይ ከፍተኛ አስተዋፅዖ አድርገዋል በሚል ሙጋቤ ጥያቄዉን አልተቀበሉትም።
ብዙዎች በመገናኛ ብዙሀን እና በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ላይ አዲሱ የዝምባቡዌ መንግስት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ለፍትህ ይቀርቡ ዘንድ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመልሳቸዉ እየተማፅኑ ይገኛሉ።
ይህ በሕግ ዓይን እንዴት እንደሚታይ በለንዶን ስኩል ኦፍ ኤኮኖሚክስ የሕግ ረዳት ፕሮፌሶር ዶክተር አዎል ቃስም አሎ እንዲህ ያስረዳሉ፣«በዓለም አቀፍ ወንጀል ለተጠረጠሩ ግለሰቦች ተገን የምትሰጥ አንዲት ሉዓላዊ አገርን ተጠያቂ የምታደርግበት የሕግ ሂደት የለም። ሰዎች የዘነጉት ግን ዚምባብዌን አሁንም እያስተዳደረ ያለዉ የበፊቱ ፓርቲ መሆኑ እና አሁንም ስልጣኑን የተቆጣጠሩት ግለሰቦች ከሙጋቤ ጋር በቅርብ ሲሰሩ የነበሩ መሆናቸውን ነው።»
በኢትዮጵያ መንግስት በኩልም ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ወደ አገር እንዲመለሱ በዚምባብዌ መንግሥት ላይ የተደረገዉ የፖለቲካ ጫና በቂ እንዳልነበረ ጠበቃና በርዋንዳ ዓለም አቀፋዊ የወንጀለኞች መዳኛ ፍርድ ቤት ዋና አቃቤ ህግ የነበሩት ዶክተር ያዕቆብ ሃይለማርያም ገልጸዋል። በወንጀል የተከሰሱ 73 የደርግ ባለስልጣናት ፍርድ ቤት ቀርበው ብይን ሲተላለፍባቸው፣ ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ግን በሌሉበት በሞት እንዲቀጡ መበየኑ እስካሁን ከፍትሕ እንዲያመልጡ አስችሏቸዋል ይላሉ ዶክተር ያዕቆብ።
«የዚምባብዌ ባለሥልጣናት መንግስቱን አሳልፈው ይሰጣሉ ብሎ መጠበቅ በጣም የማይመስል ነዉ። መንግስቱ ለዝምባቡዌ ነፃነት ላደረገዉ አስተዋፅዖ ውለታ አለባቸዉ። በዚህ ዘመን ወንጀለኛዉ በሌለበት ዉሳኔ ማሳለፍ አይደገፍም። ሰዎች ፍርድ ቤት ቀርበው ራሳቸውን መከላከል አለባቸው፣» ስሉም አክሎበታል።
አሁንም በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ኮሎኔል መንግስቱ ወደ ፍትህ እንዲቀርቡ ለማድረግ ብዙም ፍላጎት ያለ እንደማይመስላቸው የገለጹት ዶክተር አዎል ያሁኑ መንግሥት ከኮሎኔል መንግስቱ አስተዳደር ያን ያህል አይለይም ይላሉ። «የኢትዮጵያ መንግስት ራሱ እንዳለፈዉ መንግስት አምባገነን እና ጨቋኝ እየሆነ መጥቷል።»
የዝምባቡዌ የመገናኛ ብዙሃን አዉታሮች የምናንጋግዋ መንግስት መንግስቱን ወደ ኢትዮጵያ የመመለስ እቅድ እንደለለዉ ሰሙኑን ዘግበው ነበር ። ሆኖም አንድ የጀርመን ዜና አገልግሎት ዛሬ እንደዘገበው አዲሱ መንግሥት ኮሎኔል መንግሥቱን ለኢትዮጵያ አሳልፎ እንደማይሰጥ አስታውቋል።
መርጋ ዮናስ
አርያም ተክሌ