1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኬንያ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ታሳድር፤ ሒውማን ራይትስ ዎች

ቅዳሜ፣ መጋቢት 15 2010

የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሒውማን ራይትስ ዎች ኢትዮጵያ የገጠማትን የፖለቲካ ቀውስ ለመፍታት የሚያስችሉ የማሻሻያ ርምጃዎች እንዲወሰዱ ኬንያ ጫና ማሳደር አለባት ሲል ጥሪ አቀረበ። ድርጅቱ ዛሬ ባወጣው መግለጫ የኬንያ ሹማምንት ዜጎች ቀያቸውን ጥለው እንዲሰደዱ ባስገደዳቸው የኢትዮጵያ ጦር ርምጃ ላይ ሥጋታቸውን በአደባባይ መናገር ይገባቸዋል ብሏል። 

https://p.dw.com/p/2uv90
Süd Sudan Gipfel im Präsidentenpalast von Addis Abeba
ምስል Yohannes G/Eziabhare

የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቹ ሒውማን ራይትስ ዎች ኢትዮጵያ የገጠማትን የፖለቲካ ቀውስ ለመፍታት የሚያስችሉ የማሻሻያ ርምጃዎች እንዲወሰዱ ኬንያ ጫና ማሳደር አለባት ሲል ጥሪ አቀረበ። ድርጅቱ ዛሬ ባወጣው መግለጫ እንዳለው የኬንያ ሹማምንት ዜጎች ቀያቸውን ጥለው እንዲሰደዱ ባስገደዳቸው የኢትዮጵያ ጦር ርምጃ ላይ ሥጋታቸውን በአደባባይ መናገር ይኖርባቸዋል። 

የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ቀውስ በኬንያ ላይ ከፍተኛ የጸጥታ እና ሰብዓዊ ቀውስ ጫና እንደሚኖረው የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ሒውማን ራይትስ ዎች ገለጿል። ድርጅቱ "ኬንያ በኢትዮጵያ እየሆነ ያለውን በጥሞና ልትከታል ይገባል" ብሏል። 

በኢትዮጵያዋ የሞያሌ ከተማ የጸጥታ ኃይሎች በስሕተት ባሉት እርምጃ 10 ሰዎች ከተገደሉ በኋላ 10,000 ገደማ ዜጎች ወደ ኬንያ መሰደዳቸው አይዘነጋም። በኢትዮጵያ የተከሰተው የጸጥታ መጓደል ድንበር ሊሻገር እንደሚችል ሥጋቱን የገለጠው ሒውማን ራይትስ ዎች በኢትዮጵያ በተባባሰው ግጭት የሚፈጠረው ሰብዓዊ ቀውስ ለሁለቱም አገሮች ሥጋት ነው ብሏል። 

Human Rights Watch Logo Flash-Galerie
ምስል Human Rights Watch

በኢትዮጵያ ግጭት ከተባባሰ አብዛኞቹ ተጋላጭ ዜጎች መጠጊያ መሻታቸው የማይቀር መሆኑን ድርጅቱ ዛሬ ባወጣው ሐተታ ገልጿል። በዝምድና፣ በሁለቱ አገሮች መካከል ባለው የሰዎች ሽግግር ሰንሰለት እና በኬንያ ያለው የተሻለ የጸጥታ ሁኔታ ከኢትዮጵያ ለሚፈናቀሉ ዜጎች ኬንያን ተመራጭ መዳረሻ ሊያደርጋት ይችላል ብሏል ድርጅቱ። 

ድርጅቱ እንዳለው የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃነት እንዲንቀሳቀሱ፣ መገናኛ ብዙኃንና መንግሥታዊ ያልሆኑ ቡድኖች በገለልተኝነት እንዲሰሩ መፍቀድን ጨምሮ ኢትዮጵያ ቁልፍ ማሻሻያዎች እንድታደርግ ኬንያ ከምሥራቅ አፍሪቃ አገራት ቀዳሚ ሚና ሊኖራት ይገባል። የኬንያ መሪዎችም ዜጎች ወደ ኬንያ እንዲሰደዱ ባስገደዳቸው የኢትዮጵያ ጦር እርምጃ ላይ ሥጋታቸውን በአደባባይ ሊናገሩ ይገባል። 

ኬንያም ሆነች የምሥራቅ አፍሪቃ አገራት የተረጋጋችና የበለጸገች ኢትዮጵያ ታሻቸዋለች ያለው የሒውማን ራይትስ ዎች መግለጫ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ዜጎች ለውጥ እንዲመጣ በሚያቀርቡት ጥያቄ እንደ ኬንያ ያለ አመኔታ የሚጣልበት አጋር ሀገር ድምጽ ወሳኝ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብሏል። 

እሸቴ በቀለ

ማንተጋፍቶት ስለሺ