ኤደን ተኬ እና የንግድ ስኬቶቿ
ዓርብ፣ መስከረም 19 2010ማንኛውም ወጣት ራሱን ማስተዳደር የሚችልበት ስራ እንዲኖረው ይሻል። ይህንን ፍላጎት ለማሳካት አንዳንዶች ተቀጥረው መስራትን እንደ አማራጭ ይዘው ሲነሱ፣ ሌሎች የራሳቸውን ሀሳብ፣ ፈጠራ እና ህልም እውን ለማድረግ የግል ድርጅት ይከፍታሉ። ናዝሬት ከተማ ተወልዳ ያደገችው ኤደን ተኬ ወደ አዲስ አበባ ሄዳ ትምህርቷን ስትከታተል ወደፊት የት እና ለማን እሰራለሁ የሚለው አላሳሰባትም ነበር። ምክንያቱም ተመርቄ ስራ አገኛለሁ የሚል እምነት ስለነበራት። ይህ ግን ሳይሆን ቀረ። ከዛም አንድ የምታውቀው ሰው ንግድን መከራት።
ኤደንም የተሰጣትን ምክር ተከትላ፤ ደብረዘይት ወይም ቢሾፍቱ ከተማ በመግባት ሱቅ ትከፍታለች። ለመጀመርም ብዙ ነገር እንዳላስፈልጋት ኤደን ትናገራለች። የነበራት አንድ የፎቶ ኮፒ ማሽን እና አንድ ኮምፒውተር ብቻ ነው።
ለነጋዴዋና ባለቤቷ ነገሮች እየተሻሻሉ ሲሄዱም ለአካባቢው አስፈላጊ ነው ብለው ያመኑበትን የኢንተርኔት አገልግሎት ይሰጡ ጀመር። ይሁንና የሆነ ጊዜ አዋጪ ሆኖ ስላላገኙት ትተውታል። ኤደን በንግዱ ዘርፍ ስትተዳደር መጀመር ወይም አዋጪ ሆነው ያላገኛቸውን ነገሮች መተው እንደነበረባት ተናግራለች። ታድያ ፉክክሩ የጠነከረበት የንግዱ ዘርፍን ተቋቁማ አሁን የደረሰችበት ቦታ ለመድረስ ሚስጥሯ ወይም ዘዴዋ ምን ነበር? እሷ እንደምትለው ብዙ ትርፍ ከመጠበቅ ዋጋ ቀንሶ ብዙ ቁጥር መሸጥ የተሻለ ነው።
ኤደን ከቅርብ ጊዜ አንስቶ ደግሞ የንግድ አቅጣጫዋን በከፊል መቀየሯን ትናገራለች። ይኼውም ጎን ለጎን የፅዳት እቃዎች እሸጣለሁ ይላለች። ኤደን ከትምህርት ቤት በቀጥታ ወደግል ስራ ነው የገባቸው። ተቀጥራ ሰርታ አታውቋም። ተቀጥሮ ከመስራት ጋር የራስ አለቃ ሆኖ መስራቱን ለማመዛዘን ኤደን እድል ባታገኝም የስራ ኃላፊነቱን በሚገባ እንደተወጣችው ታምናለች።
ኤደን ደብረ ዘይት ወይም ቢሾፍቱ ከተማ ሱቅ የከፈተችው ከምታውቀው ሰው ባገኘችው ምክር እንደሆነ ቀደም ሲል ተናግራለች። እሷስ ሌሎች በግል ስራ ለመሰማራት ሀሳቡ ላላቸው ወጣቶች ምን ትመክራለች? የወደፊት እቅዷስ ምንድን ነው? የድምፅ ዘገባውን ተጭነው የነበረንን ቆይታ ያድምጡ።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሀመድ