ኢትዮጵያውያን ሐጃጆች በሳዑዲ አረቢያ
ሰኞ፣ ነሐሴ 14 2010የኢድ አል-አደሐ አረፋ በዓል በነገው ዕለት ይከበራል። ጠቅላይ ምኒስትር አብይ አሕመድ ለመላው የእስልምና ዕምነት ተከታዮች የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ጠቅላይ ምኒስትሩ በዛሬው ዕለት ባስተላለፉት መልዕክት "አረፋ በዓል የመስጠት፣ የደግነትና የቸርነት በዓል በመሆኑ የተቸገሩና አንዳች ጥሪት የሌላቸው ወገኖቻችንን በመርዳት በመልካምና ደግ ሥራ በዓሉን ከተቀረው ወገኖቻችን ጋር በጋራ እንድናከብር ጥሪዬን አቀርባለሁ" ብለዋል። ጠቅላይ ምኒስትር አብይ "በሀገራችን የዘመናት የአብሮነት ታሪክ ውስጥ መቻቻል፣ መተዛዘን እና መረዳዳት ያለውን ፋይዳ በውል የሚረዳው የሀገራችን ሙስሊም ማኀበረሰብ በሠው ልጅ የዘመናት ጥረትና ድካም የዘረጋናቸውን መልካም እሴቶች ኃላፊነት የማይሰማቸው አካላት በአንድ ጀንበር እንዲንዷቸው ብሎም ወደስርዓት አልበኝነት እንዲቀይሯቸው ፈጽሞ እንደማይፈቅድ እምነቴ ጽኑ ነው" ሲሉም አክለዋል። ለምሁራን፣ የአገር ሽማግሌዎች እና የእምነት አባቶች "የማህበረሰባችሁ የእውቀት ቀንድ ናችሁና ሥርዓት አልበኝነት እንዳይሰለጥን ማኀበረሰባችሁን በሞራልና በሥነምግባር ተግታችሁ እንድታንጹ" ሲሉ መልክት አስተላልፈዋል። ሳዑዲ አረቢያ የሚገኘው ነብዩ ሲራክ ደግሞ የዕምነት ግዴታቸውን ሊወጡ መንገድ የገቡ ሐጃጆችን አነጋግሯል።
ነብዩ ሲራክ
እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሀመድ