ኢሕአዴግ «በሓቅ» መደራደር አለበት፣ ዶክተር መረራ
ረቡዕ፣ ጥር 16 2010በኢትዮጵያ ዉስጥ የሚገኙት ተቃዋም ፓርቲዎች በአሁኑ ግዜ ከገዥዉ ፓርቲ ጋር የፓርቲ ምዝገባ፣ የፀረ-ሽብር ህጎች ላይ ማሻሽያ ማድረግን ጨምሮ በተለያዩ የፖለቲካ ነጥቦች ላይ ድርድር ላይ ይገኛሉ። የፀረ-ሽብር ህጉ የፖለቲካ ምህዳሩን አጥበዋል በሚል ምክንያት በነገዉ እለት ድርድሩ እንደሚቀጥል በድርድሩ ላይ እየተሳተፉ ያሉት የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ የሕዝብ ግኑኙነት ሃላፊ አቶ ወንድወሰን ተሾመ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። አቶ ወንድወሰን ተሾመ መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የገባዉ ቃል «አስተማማኝነት» ይጎድለዋል ይላሉ።
ይሁን እንጅ ኦፌኮን ጨምሮ ሌሎችም የመደረክ አባል ፓርቲዎች እንድሁም ሰማያዊ ፓርቲ በድርድሩ ሂደት ላይ ከገዥዉ ፓርቲ ኢሕአዴግ ጋር ባለመስማማታቸዉ ከድርድሩ ወተዋል። ድርድሩ እነዚህን ፓርቲዎች ሳያካትት ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግ በቅርቡ «ብሔራዊ መግባባት መፍጠር» እንዲሁም «የፖለቲካና የዴሞክራሲ ምሕዳሩን ማስፋት» እንደሚፈልግ ቃል መግባቱ ጋር ይፃረራል ሲሉ የሚከራከሩ አሉ። የኦፌኮዉ ሊቀመንበር ዶክተር መረራ ግን ገዥዉ ፓርቲ ከሕዝብ ድጋፍ ካላቸዉ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር «በሓቅ» መደራደር አለብት ብለዋል።
በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና የዉጭ ግንኝነት መምህር አቶ ዳንኤል መኮንን ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግ ስለ «ብሔራዊ መግባባት መፍጠር» እንዲሁም «የፖለቲካና የዴሞክራሲ ማኅዳሩን ማስፋት» የምንናገራቸዉና ተግባራዊ የምያደርጋቸዉ የተለያዩ ናቸዉ ይላሉ።
የኢትዮጵያ መንግሥት አገሪቱ ዉስጥ ካሉት «የህዝብ ድጋፍ» ካላቸዉ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ድርድር ካላደረጉ አስከፊ ተቃዉሞ ተመልሶ ልያገረሽ እንደሚችልም ማስጠንቀቃቸዉ የዜና አዉታሮች ዘግበዋል።
መርጋ ዮናስ
አዜብ ታደሰ