አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ የኢትዮጵያ ፕሬዚደንት ሆነው ተሰየሙ።
ሐሙስ፣ ጥቅምት 15 2011አምባሳደር ሳህለወርቅ በገዛ ፈቃዳቸው ስልጣናቸውን የለቀቁትን ፕሬዚደንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመን ይተካሉ።ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ ሀላፊነታቸውን የለቀቁት የስራ መልቀቂያቸውን ዛሬ ለሁለቱ ምክር ቤቶች ስብሰባ ላይ በማቅረብ ነው ። የሀገሪቱ የመጀመሪያ ሴት ፕሬዚደንት ሆነው የተመረጡት ፣ በዲፕሎማትነት ሰፊ የስራ ልማድ ያላቸውአምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ በተለያዩ ሀገራት አምባሳደር በመሆን ያገለገሉ ሲሆን፣ ከጎርጎሪዮሳዊው 1989 እስከ 1993 በሴኔጋል የኢትዮጵያ አምባሳደር፣ እንዲሁም፣ ከ1993 እስከ 2002 በጂቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደር እና በምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት፣ኢጋድ የኢትዮጵያ ቋሚ መልእክተኛ በመሆን ሰርተዋል። አምባሳደር ሳህለወርቅ ሁሉንም ወገኖች በማቀራረብ ባለፉት ወራት በሀገሪቱ የታዩትን ብሔር ተኮር ግጭቶች ለማብቃት እና ሰላም ለማውረድ ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
የመጀመሪያው የስልጣን ዘመናቸው ሊያበቃ አንድ ዓመት ሲቀረው ስልጣናቸውን የለቀቁት ፕሬዚዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ በርእሰ ብሄርነት ያገለገሉባቸው ያለፉት አምስት ዓመታት በህይወት ጉዟቸው ትልቅ ቦታ የሚይዝ መሆኑን መልቀቂያቸውን ለምክር ቤቶቹ ባቀረቡበት ወቅት ባደረጉት ንግግር ገልጸዋል።
ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር
ጌታቸው ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
አርያም ተክሌ
ማንተጋፍቶት ስለሺ