1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ትኩረት የሚሻው የእናቶች ጤና

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 30 2010

እናትነት ወልዶ ልጅን ማቀፍ ብቻ ሳይሆን ወደዚያ የሚያደርሰው የምጥ ስቃይም የሚታሰብበት ነው። የሕክምና ርዳታ እንደልብ በማይገኝባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ነፍሰጡሮች ልጅን በመውለድ ሂደት ለተለያዩ ችግሮች እንደሚዳረጉ የሚታይ የሚሰማ ጉዳይ ነው።

https://p.dw.com/p/2xNlc
Symbolbild - Schwangerschaft
ምስል picture-alliance/dpa/F. Heyder

በባለሙያ ርዳታ የሚወልዱ እናቶች ብዙ አይባሉም፤

በተመድ ከተቀረጸው ዘላቂነት ያለው የልማት ግቦች በወሊድ ወቅት ሕይወታቸውን የሚያጡ እናቶችን ቁጥር መቀነስ አንዱ ነው። ምንም እንኳን ኢትዮጵያ ይህን ግብ ለማሳካት ከፍተኛ ጥረት ከሚያደርጉ አዳጊ ሃገራት ተርታ ብትሆንም፤  አብዛኛዉ ሕዝቧ በከተማ አካባቢ የሚኖር ባለመሆኑ ሀኪም ቤት ውስጥ በዘርፉ በሰለጠኑ ሃኪሞች እጅ የመውለድ ዕድሉ ያላቸው ዛሬም ብዙ የሚባሉ አይደሉም። የሃኪም ቤቶች ርቀት አንድ ነገር ሆኖ የተለያዩ መረጃዎችን በሚያራጩት እንደፌስ ቡክ ያሉ ማኅበራዊ መገናኛ ብዙሃን አሳዛዥና አስደንጋጭ የመውለድ ሂደት ገጠመኞችም አልፎ አልፎ ይነበባሉ። ኢትዮጵያ የጤና አገልግሎት እየሻሻለ እና እየተስፋፋ ካለባቸው አዳጊ ሃገራት ተርታ የምትጠቀስ ሀገር ሆናለች። በተለይ የስነተዋልዶ ጤናን በተመለከተ ኅብረተሰቡ በአሁኑ ጊዜ ሀኪምቤት መውለድ ያልተጠበቁ አስደንጋጭ አጋጣሚዎችን ስጋት ሊቀንስለት እንደሚችል እየተገነዘበ መምጣሉት ለዶቼ ቬለ ኃትስአፕ መስመራችን ከደረሱን አስተያየቶች መረዳት ይቻላል። ግን ደግሞ ይላሉ አስተያየት ሰጪዎቹ በሀኪም እጅ የመገላገሉ ፍላጎት ቢኖርም የቦታው ርቀት የአገልግሎቱ ደረጃ ዝቅ ማለት ብዙ ነፍሰጡሮች በቤት ውስጥ እንዲገላለገሉ አስገድዷቸዋል የሚሉና የመንገድ ርቀትን የባለሙያ እጥረትን የሚያሳዩ በርከት ያሉ አስተያየቶች ናቸው የደረሱን። ከአስተያየቶቹ አብዛኞቹ ከእናቶች የጤና አገልግሎት አኳያ አማራ ክልል ውስጥ ይታያል ያሉትን ጉድለት የሚጠቆሙ በመሆናቸው ወደክልሉ የጤና ቢሮ ደወልን። በአማራ ክልል ጤና ቢሮ የፈውስ ሕክምና እና ተሐድሶ አገልግሎት የሥራ ሂደት ባለቤት የሆኑት አቶ አበበ ዳኘውን አገኘን። ከእሳቸው እንደተረዳነው በክልሉ እስከ 22 ሚሊየን የሚደርስ ሕዝብ አለ ተብሎ ይገመታል፤ ለዚህ ሕዝብም በተለይ ለእናቶች እና ሕጻናት የጤና አገልግሎት የሚሰጡ ጤና ጣቢያዎች እና የመጀመሪያ ደረጃ ሃኪም ቤቶች አሉ። በመቶዎች የሚቆጠሩ የጤና ኬላዎችም እንዲሁ። እስከኅብረተሰቡ በወረደው የጤና ኤክስቴንሽን ስልትም ለነፍሰጡር እናቶች ተገቢዉ ትምህርት እና ክትትል እንደሚደረግ ይናገራሉ ኃላፊው። ለመውለድ የደረሱ ነፍሰጡሮችን በአቅራቢያቸው በሚገኙ የጤና ኬላዎች ማዋለድ የማይቻል ሲሆን ደግሞ በቅብብሎሽ ስርዓቱ መሠረት ለከፍተኛ የህክምና ርዳታ ወደሃኪም ቤቶች የሚሻገሩበት መስመርም ተዘርግቶ እየተሰራበት መሆኑንም አክለው ገልጸዋል። ለዚህ አገልግሎትም ከ400 የሚበልጡ አምቡላንሶች ክልሉ እንዳሉትም አቶ አበበ ዘርዝረዋል። ኅብረተሰቡ ስለሚያገኘው የሕክምና ሆነ የአምቡላንስ አገልግሎት ሁኔታ በኋትስአፕ የተላኩልንን አስተያየቶች አንስተን እንዴት ይመዝኑታል አልናቸው አቶ አበበን። ዝርዝሩን ከድምፅ ዘገባው ያድምጡ፤

Afrika Mutter und Kind Baby Symbolbild
ምስል Fotolia/poco

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ