1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ገጣሚ፤ ሐያሲ፤ ጋዜጠኛ እና መምሕሩ ሶሎሞን ዴሬሳ ሲታወስ

ዓርብ፣ ኅዳር 1 2010

ሥመ-ጥሩው ሶሎሞን ዴሬሳ ለዓመታት በኖረባት፣ ባስተማረባት ምኒያፖሊስ ባለፈው ሳምንት ከዚህ ዓለም ተሰናበተ። 80 ዓመቱ ነበር። በራሱ ብዕር በዘበት እልፊቱ የግጥም መግቢያ እንዳሰፈረው ያረፈው "ሳይገፈተር፣  ሳይፈተሽ መለዮ ለባሽ ሳይጮህበት፣ የመስራት እድል" ባገኘበት አገር ነው።

https://p.dw.com/p/2nNBC
Symbolbild Buch Bücher Lesen
ምስል Colourbox

ሶሎሞን ደሬሳ

ሶሎሞን በኢትዮጵያ "ልጅነት" እና "ዘበት እልፊቱ ወለሎታት" በሚል ርዕስ ባሳተማቸው ሁለት የግጥም መጻሕፍት ይታወቃል። የተወለደው በምዕራብ ወለጋ ዞን ከጊምቢ አቅራቢያ ከምትገኘው ጩታ በተባለች መንደር ነዉ። "የማንበብ ፍላጎቴ የመጣው ሰነፍ ተማሪ ስለበርኩኝ ነው" ይል የነበረው ሶሎሞን ከትውልድ መንደሩ ርቆ የተጓዘው ግን ገና የ4 አመት ልጅ ሳለ ነው። በ16 አመቱ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብቶ ስነ-ጽሁፍ እና ፍልስፍና አጥንቷል።

ወደ ፈረንሳይ ተጉዞ በቱሉዝ ከተማ ከሥመ-ጥር ጸሐፊያን፤ ሰዓሊያን እና የሙዚቃ ሰዎች ጋር ወዳጅነት መስርቷል። በኢትዮጵያ ራዲዮ እና ቴሌቭዥን ድርጅት የእንግሊዘኛ ዜና አንባቢነት፣ የፕሮግራም አዘጋጅነት እና ምክትል ሥራ አስኪያጅነት አገልግሏል። አዲስ ሪፖርተር፣ ኢትዮጵያን ኦብሰርቨር እንዲሁም መነን በተባሉ መፅሔቶች ሐተታዎችን ይፅፍም ነበር።

ሰለሞን በ1965 ዓ.ም. በተጓዘባት አሜሪካ የምሥራቃውያን ፍልስፍና እና የአሜሪካን ስነ-ጽሁፍ በማጥናት የመጀመሪያ ዲግሪውን አግኝቷል። ወደ አሜሪካ ሲያቀና አገር እየዞረ የማየት እቅድ ነበረው። በመጨረሻም ወደ ኢትዮጵያ ሊመለስ።

በሚኒሶታ እና በሜትሮፖሊታን ስቴት ዩኒቨርሲቲዎች በመምህርነት አገልግሏል። ለአሜሪካ በጎ ፈቃደኞች አማርኛ እያስተማረ ፕሮፌሰር ውልፍ ሌስላው መዝገበ ቃላት ሲያዘጋጁ ተሳትፎ ነበረው። ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ሰነዶችን ከእንግሊዘኛ ወደ ፈረንሳይኛ የመተርጎም ሥራ ሰርቷል። ለድርጅቱ ራዲዮም ያገለግል ነበር።

ሶሎሞን ጉጉ አንባቢ ነበር። ፍልስፍና፤ ሒሳብ፣ ፊዚክስ፣ ሐይማኖት፣ስነ-ፅሁፍ የመሳሰሉትን። እንዳለጌታ ከበደ እንደሚለው የሶሎሞንን ግጥሞች ለመረዳት የመፃህፍቱን መግቢያዎች በጥሞና ማንበብ ያሻል። እውነትም መግቢያዎቹ ለምን መፃፍ እንደሚሻ ፍንትው አድርገው ያሳያሉ።

በዘበት እልፊቱ ወለሎታት መግቢያ ሶሎሞን "ግጥም ሲዋጣ ስንኝ ይገጥማል፤ ቤት ይመታል፤ ዜማ ያነበንባል፤ ቋንቋ ይፈነድቃል። ተረት ይተረታል። ታሪክ እልባት ያገኛል። ሙሾ ይወርዳል። ለፍቅር ግምጃ ይገባል። ግጥምን የሚያረክሰው ያንዳንድ መስመሮች መበላሸት ሳይሆን የሃሳብ ወይንም የስሜት ሀቅ ማጣት ወይንም ለገጣሚው ባይተዋር መሆን ነው።" ሲል አስፍሯል።

ሙሉ መሰናዶውን ለማዳመጥ የድምፅ ማዕቀፉን ይጫኑ