በኦሮምያ የአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም ረቂቅ አዋጅ
እሑድ፣ ሐምሌ 2 2009በኢትዮጵያ ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባ የኦሮምያን ልዩ ጥቅም ያስከብራል የተባለው እና በኢትዮጵያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ፀድቆ ባለፈው ሳምንት ለኢትዮጵያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተመራው ረቂቅ ህግ እያነጋገረ ነው። ረቂቁ የኢትዮጵያ ህገ መንግሥት አንቀፅ 49 ንዑስ አንቀጽ 5 ላይ ኦሮምያ ከአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም ማግኘት እንደሚገባት በተደነገገው መሠረት መዘጋጀቱን የሚኒስትሮች ምክር ቤት አስታውቋል።
ከ2006 ዓም ጀምሮ እስካለፈው መሥከረም ድረስ በተለይ በኦሮምያ መሥተዳድር ለተነሳው ሕዝባዊ ተቃውሞ አንዱ ምክንያት በአዲስ አበባ እና አካባቢዋ የሚገኙ የኦሮሞ ተወላጆች ፣ በ1987 ዓም የፀደቀው ህገ መንግሥት ውስጥ የሰፈረው የዚህ መብት ተጠቃሚ አልሆኑም የሚል ነበር። ተቃውሞው ባስከተለው ግጭት በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ዜጎች ተገድለዋል። ንብረትም ወድሟል።
በህገ መንግሥቱ የሰፈረውን ልዩ ጥቅም ያስከብራል ተብሎ ከ22 ዓመት በኋላ የቀረበውን ረቂቅ ህግ የዘገየ፣ እንደሚነገርለትም የኦሮምያን ጥቅም ለማስጠበቅ ተብሎ ሳይሆን ህዝቡን እርስ በርስ ለማጋጨት ያለመ ነው የሚሉ እና ሌሎችም ትችቶች ይቀርቡበታል። መንግሥት ረቂቅ አዋጁ ቢዘገይም የመንግሥትን ሕዝባዊነት የሚያሳይ ነው ሲል ይከራከራል።
አነጋጋሪው «በኦሮምያ የአዲስ አበባ ልዩ ጥቅም ረቂቅ አዋጅ» የዛሬው እንወያይ ርዕስ ነው በዚህ ርዕስ ላይ የሚወያዩ አራት እንግዶች ጋብዘናል እነርሱም አቶ ጥሩነህ ገምታ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ በምህጻሩ ኦፌኮ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል፣ አቶ ተማም አባቡልጉ ጠበቃ እና የህግ ባለሞያ አቶ በትሩ ዲባባ በረቂቅ ህጉ ላይ ጥናት ያካሄዱ የህግ ባለሞያ እንዲሁም አቶ ብርሀነ መስቀል አበበ በአሜሪካን ሀገር ነዋሪ የሆኑ የህግ የፖሊሲ እና የቢዝነስ አማካሪ ናቸው። በዚህ ውይይት ላይ የኦሮምያ ክልላዊ መንግሥት ባለሥልናት እንዲሳተፉ ዶቼቬለ ቢጋብዝም የክልሉ መንግሥት ህዝብ ግንኙነት ረቂቁ ወደፊት ህዝብ እንዲወያይበት ስለሚደረግ ከዚያ በፊት ስለ ረቂቁ በመናገር በህዝቡ ላይ ተጽዕኖ ላለማሳደር በውይይቱ ላለመካፈል አቋም መያዙን ገልጸውልናል። ሙሉውን ውይይት የድምጽ ማዕቀፉን በመጫን ማዳመጥ ይቻላል።
ኂሩት መለሰ
ልደት አበበ