1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሼክ መሐመድ አል-አሙዲ ተፈተው ይሆን?

ማክሰኞ፣ ኅዳር 5 2010

ሳዑዲ አረቢያ ያሰረቻቸው ልዑላን እና የናጠጡ ሐብታሞች እጣ-ፈንታ በግልፅ ባይታወቅም አዲስ አበባ ላይ ሼክ ሙሐመድ አል-አሙዲ ሊፈቱ ነው የሚል ወሬ ይናፈሳል። በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የተናፈሰው ወሬ ከሼኩ ድርጅት አቅራቢያ የተሰማ ነው ቢባልም የተረጋገጠ ምንጭ ግን የለውም።

https://p.dw.com/p/2nYBB
Ritz-Carlton in Saudi Arabien
ምስል picture-alliance/dpa/M. Kappeler

የሳዑዲ አረቢያ የእስር ዘመቻ ዛሬም ያነጋግራል

በሳዑዲ አረቢያው አልጋ ወራሽ የሚመራው የጸረ-ሙስና ኮሚቴ የወሰደው እርምጃ ዛሬም እያነጋገረ ይገኛል። ከስድስት ወራት በፊት በሙሰኞች ላይ ጠበቅ ያለ እርምጃ ሊወስዱ የዛቱት የ32 አመቱ ልዑል ከበርቴዎችን ብቻ ሳይሆን ልዑላን እና ምኒስትሮችንም አልማሩም። ከ200 በላይ ሰዎች የታሰሩበት ዘመቻ ግን ብዙዎች የጠበቁት ማዕበል አልነበረም።

የአገሪቱ ጠቅላይ አቃቤ-ሕግ ባለፉት ጥቂት አስርት አመታት ቢያንስ 100 ቢሊዮን ዶላር ያላግባብ ጥቅም ላይ ውሏል ብለው ነበር። እርምጃው ልዑሉ ሥልጣናቸውን ለማጠናከር፣ ተቀናቃኞቻቸውንም ለማራቅ ያደረጉት ነው የሚሉ ትንታኔዎችም ይደመጣሉ።

ሳዑዲ አረቢያ ያሰረቻቸው ልዑላን እና የናጠጡ ሐብታሞች እጣ-ፈንታ በግልፅ ባይታወቅም አዲስ አበባ ላይ ሼክ ሙሐመድ አል-አሙዲ ሊፈቱ ነው የሚል ወሬ ይናፈሳል። በማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን የተናፈሰው ወሬ ከሼኩ ድርጅት አቅራቢያ የተሰማ ነው ቢባልም የተረጋገጠ ምንጭ ግን የለውም። ለመሆኑ ሼክ ሙሐመድ አል-አሙዲ ተፈተው ይሆን? መቀመጫውን ሳዑዲ አረቢያ ያደረገው የዶይቼ ቬለ ወኪል ስለሺ ሽብሩ እንደሚለው ግን ከወሬ በቀር ምንም የተፈታ የለም። 


ስለሺ ሽብሩ
እሸቴ በቀለ
ኂሩት መለሰ