1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ፑንትላንድና ሶማልያ

ሐሙስ፣ ጥር 1 2006

ከፊል ራስ ገዝ በሆነችው ፑንትልንድ፤ ቀድሞ በመቅዲሹ የሶማልያ ጠ/ሚንስትር የነበሩት አብዲዋሌ ሙሐመድ ዓሊ ጋስ በጋረዌ አዲስ ፕሬዚዳንት ይሆኑ ዘንድ ተመርጠዋል። የአኒህ ሰው መመረጥ ፣ ላጠቃላዩ የሶማልያ ሰላምና አንድነት ምን ዓይነት ድርሻ ይኖረው

https://p.dw.com/p/1Ao7a

ይሆን?፤ በጀርመን የማክስ ፕላንክ ተቋም፣ የፑንትልንድና ሶማልያ ጉዳዮች አጥኚ ባለሙያ የሆኑት ፣ ሄር Markus Höhne

Abdurahman Mohamed Farole Somalia ARCHIV 2009
ምስል Tony Karumba/AFP/Getty Images

ሶማልያ ከ ጥር ወር 1983 ዓ ም አንስቶ፣ አምባገነናዊ እንደነበረ ቢታወቅም ማዕከላዊ መንግሥቷ ተንዶ በተለያዩ ጦር አበጋዞች ተከፋፍላ በምሥቅልቅል ብዙ ዓመታት ማሳለፏ የሚታወስ ነው። ሶማሊላንድ ዓለም አቀፍ እውቅና ባታገኝም ራሷን የቻለች ሀገር ሆናለች። በመቅዲሹ ያለው መንግሥት በአፍሪቃ ኅብረት ሰላም አስከባሪ ኃይሎች ጥበቃ ቀስ በቀስ በማንሠራራት ላይ ይገኛል። ደቡቡ ፣ እስካሁን ሊጠፋ ባልቻለው አሸባብ ታጣቂ ኃይል እንደታመሰ ነው። ለሶማልያ ባጠቃላይ ፌደራላዊ መዋቅር እንደሚበጃት ያስገነዘበችው ከፊል ራስ ገዝ መስተዳድር ፑንትላንድ ፣ ትናንት ይህን አቋም የሚያጠናክሩ ፕሬዚዳንት መርጣለች። የምርጫው ውጤት ለሶማልያ ያለው ትርጉም ምንድን ነው? ማርኮስ ሆኧነ-«የአብዱዋሌ ሙሐመድ ዓሊ ጋስ መመረጥ እ ጎ አ በ 2009 በመቅዲሹ የሶማላያ ጠ/ሚንስትር ስለነበሩ፣ የውህደት ሰው ናቸውና ፑንትላንድንና ሶማልያን ያስተሣሥራሉ ተብሎ ነው የሚታሰበው። ባለፉት ጥቂት ዓመታት፣ ሁኔታዎች ተለዋውጠዋል። ለሶማልያም፣ ፌደራላዊ ሕገ መንግሥት ተሰናድቶ ቀርቧል። ይህ ደግሞ የፑንትላንድ ዓላማ ነበረ። እናም ፑንትላንድ የፈለገችው አወቃቀር እ ጎ አ በ 2012 ተግባራዊ ለመሆን በቅቷል። »

ፑንትላንድ ፤ እስከተጠቀሰው ጊዜ ድረስ፤ ይህን ፌደራላዊ የመንግሥት ሥርዓት ስታራምድ ብትቆይም ፤ በትናንቱ ምርጫ የተሸነፉት የቀድሞው ፕሬዚዳንት አብድራህማን ፋሮሌ ባለፈው አንድ ዓመት ከመንፈቅ ባፋጣኝ ራሳቸውን ከመቅዲሹ ማራቅ ጀምረው ነበር። ከመቅዲሹ ማፈንገጡም ቀጥሎ ባለፈው ነሐሴ ግንኙነቱን ከአነአካቴው አቋርጠው እንደነበረ የሚታወስ ነው። ጋርዌና መቅዲሹ(ፑንትላንድና ሶማልያ)አንድ ዓይነት አቋም ቢይዙም በሚያለያይ መሥመር በመጓዝ ላይ እንደነበሩ የሚታበል አይደለም።። አብድራህማን ፋሮሌ አፈንጋጩን መንገድ ይዘው ነበረና የአብድዋሌ ሙሐመድ ዓሊ ጋስ መመረጥ ለጠቅላላዋ ሶማላያ ብሥራት ነው የሆነው። ይህ ምርጫ ፣ ምናልባት ውሎ አድሮ፣ ሶማሊላንድ ወደ ፌደራላዊ አንድነት እንድትመለስ ያስችል ይሆን!?

Somalische Piraten in Bassaso
ምስል AP

«እንደ እውነቱ ከሆነ፤ በአሁኑ ቅጽበት ሶማሊላንድ ፈጽሞ ራስን ወደ መቻል፤ ደረጃ ነው የተረማመደችው። ከፑንትላንድ በስተምዕራብ የምትገኘውን ሶማሊላንድ /ሃርጌሳን በተመለከተ የአብድዋሊ መሐመድ ዓሊ ጋስ እስከዚህም በአወንታዊ መልኩ ይታያል ብሎ መጠበቅ የማይቻል ነው። እርግጥ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ከሶማሊላንድ በኩል እምብዛም ችግር አላጋጠማቸውም ነበር። በመሠረቱ ፤ በራሳቸው መደበኛ መስተዳድር (ፑንትላንድ) ላይ ነበረ ያተኮሩት ከሶማሊላንድ ጋር የቆየውን የድንበር ውዝግብም የሶልና ሳማግን አጨቃጫቂ የግዛት ይገባኛል ጥያቄ ችላ ብለውት እንደነበረ ነው የሚታወሰው። አሁን መጠበቅ የሚያሻው አብዱዋሊ መሐመድ ዓሊ ጋስ ምን እንደሚያደርጉ ነው። ለሶማልያ አንድነት ፤ ሶማሊላንድንም ጨምሮ፤ ለዚህ የቆሙ ከሆነ በሶማሊላንድና ፑንትላንድ መካከል ውዝግብ ይቀሰቀሳል ማለት ነው።»

አዲሱ ፕሬዚዳንት አብዲዋሌ ሙሐመድ ዓሊ ጋስ በተጨማሪ የፖንትላንድን የባህር ላይ ውንብድና ችግርና ከፅንፈኛ እስላማውያን ኃይሎች መላ መፈለግ ግድ ሳይሆንባቸው አይቀርም።

«እንደሚመስለኝ ፤ የባህር ላይ ውንብድና በፑንትላንድ አሁን ያን ያህል አስጨናቂ አይደለም። ባለፉት 12 ወራት የባህር ላይ ውንብድና ችግር በእጅጉ እየተወገደ ነው። ይህም የሆነው ብዙዎች የባህር ላይ ወንበዴዎች ፤ የፑንትላንድናና የሶማልያን የባህር ጠረፎች በሚጠብቁ ፣ በዓለም አቀፉ የባህር ኅይል አባላት በመመታታቸው እንዲሁም እርስ በእርስ ባደረጉት ውጊያ በመሞታቸው ነው። የተረፉትም ያን ሙያ ትተው ወደ ሌላ ንግድ ተዛውረዋል።

ያወሳኸው ፤የፅንፈኛ እስላማዊ ኃይሎች ጉዳይ ፣ ትልቁ ችግር እርሱ ነው። ከቦሳሶ በስተምዕራብ ፣ በጎሊስ ኮረብቶች ከአሸባብ የተከፈለ አንድ ቡድን በዚያ መሽጎ የፑንትላንድ ሲቭሎችንና ፀጥታ አስከባሪዎችን በቦሳሶ ዙሪያ ያጠቃ ነበረ። እንዳለፈው ጊዜ ሁሉ ብርቱ ሳንክ እንደፈጠረ ነው። አሸባብ በደቡብ ሶማላያ ይዞታው ምን ይሆናል?አሸባብ ገና አልተሸነፈም። የሚቆጣጠረው ግዛት አለ። በሶማልያ ብቻ ሳይሆን ባካባቢው፤ በኬንያም እንደታየው አደጋ የመጣል ችሎታ አለው በኢትዮጵያም ቢሆን፤ በከፊል!።»

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ