ፀረ መንግሥት ተቃውሞ በኢትዮጵያ
ቅዳሜ፣ ሐምሌ 30 2008የዛሬውን የተቃውሞ ሰልፍ የጠሩት የኦሮሞ ተቃውሞ ፓርቲዎች መሆናቸውን ዜና ወኪሉ አመልክቶዋል። ግዙፍ የፖሊስ ስምሪት በተደረገበት በመስቀል አደባባይ በተካሄደው ተቃውሞ ሰልፍ ላይ የተገኙት ወደ 500 የሚጠጉ ሰልፈኞች «ነፃነታችንን እንፈልጋለን፣» «የፖለቲካ እስረኞቻችን ይፈቱልን፣» እና ሌሎች መሰል መፈክሮችን አሰምተዋል። ፖሊስ ተቃውሞውን ወዲያው መበተኑን ተያይዞ የወጣው ዜና አስታውቋል።የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የብሔራዊ አንድነትን የሚያሰጉ የተቃውሞ ሰልፎች እንዳይደረጉ ትናንት እገዳ በማሳረፍ፣ ፖሊስ ተቃውሞውን ለማከላከል ባለው ኃይል ሁሉ እንዲጠቀም ጥሪ አስተላልፈዋል።የተቃውሞ ሰልፎች በሌሎች የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎችም መካሄዳቸውን የዓይን እማኞች ለዶይቸ ቤለ ነግረዋል። በተያያዘ ዜናም፣ በጎንደር ከተማ ትናንት በተካሄደ ተቃውሞ ወቅት በተፈጠረ ግጭት ሁለት ሰዎች መሞታቸውን የዜና ምንጭ ሮይተርስ ዘገባ አስታወቀ። ግጭቱ የተነሳው ፖሊስ የወልቃይት ጠገዴን የማንነት እና የድንበር ጥያቄን በተመለከተ የተጀመረ የተቃውሞ ዘመቻመሪዎች ከሆኑት አንዱን ወደ ፍርድ ቤት ባቀረበበት ጊዜ እንደነበር አንድ ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ በቦታው የነበረ ግለሰብ ለዜና ምንጭ ሮይተርስ ገልጾዋል። የአማራ ክልል መስተዳድር ኃላፊ አቶ ገድሉ አንዳርጋቸው ሰው ስለመሞቱ ለጋዜጠኞች ባይናገሩም፣ ተቃውሞው ሕገ ወጥ እንደነበረ እና የፀጥታ ኃይላት በተቃውሞው በሚሳተፉ ላይ ርምጃ እንደሚወስዱ አስታውቀዋል። አንድ በስልክ ለዜና ምንጩ ቃላቸውን የሰጡ የዘመቻው አባል በጎንደር መሀል ከተማ ሁለት ሰዎች በጥይት ተኩስ መገደላቸውን ገልጸዋል። በተያያዘ ዜና፣ የሰማያዊ ፓርቲ ለነገ በባህር ዳር ከተማ ጠርቶት የነበረ ተቃውሞ ሰልፍ መሰረዙን የአዲስ አበባ ዘጋቢያችን ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር ቀደም ሲል በስልክ ገልጾልናል።
አርያም ተክሌ
እሸቴ በቀለ