አፍሮ-ጀርመን
ዓርብ፣ ሚያዝያ 6 2009« ሁልጊዜ ከየት ነው የመጣችሽ የሚለው ጥያቄ! ከሐምቡርግ ከተማ ስል ፤ መልሴ ተቀባይነት አያገኝም ። ቀጣይ ጥያቄ ይኖረዋል። ግን ቀለምሽ እኮ?ይላሉ ቀለሜ ምን? ገበያ ሄጄ አልገዛውት።ቀለሜ ጀርመን ነው» ትላለች ጋዜጠኛ ያና ፓራይገስ። አፍሮ-ጀርመን ስለሚለው የዘጋቢ ፊልሟ ስትናገር። ፊልሙ ጥቁር ሆኖ ጀርመን ሀገር መኖር ምን ማለት እንደሆነ ይቃኛል። ለዚህም የተለያዩ እና ሁለት የጋራ ነገር የሚጋሯት ሰዎች አነጋግራለች። ጥቁር የቆዳ ቀለም እና ሀገራቸው ጀርመን የሆኑ። ለምሳሌ እንደ ያና ሐምቡርግ ከተማ ያደገው ሙዚቀኛ ሳሚ ዴሉክስ።« ከመጀመሪያው አንስቶ ስለ እኔ ትንሽ ግራ ያጋባ የነበረው ጸጉሬ ሉጫ መሆኑ ነው። ትምህርት ቤት ልጆች እኔን « ኒገር» ብለው ሲጠሩኝ እና እኔ ስናደድ ወይም ስቆጣ ለነገሩ ጸጉርህ ሉጫ ነው። ትክክለኛ «ኒገር» አይደለህም። ይሉኝ ነበር። ያን ጊዜ እሺ ጥቁርነቴ ኒገር ሊያስብለኝ ይችላል። ነገር ግን ፀጉሬ ከርዳዳ ስላልሆነ ልበሳጭ አይገባኝም እያልኩ ራሴን ለማረጋጋት እሞክራለሁ።ብቻ ሁሉም የሚቃረን ነበር።ይህ ነው ከውጭው ይገጥመኝ የነበረው። ያና የአፍሮ-ጀርመን ዘጋቢ ፊልምን ያዘጋጀትበትን ምክንያት እንዲህ ትገልፃለች።
«ጀርመን የነጭ ሀገር እንደሆነች የሚጠቁም አፈታሪክ አለ። ይህ ልክ አይደለም። መቼም ሊሆን አይችልም። የተከፋፈለ አስተሳሰብ በሚንፀባረቅበት ባሁኑ ሰዓት ከሌላ አቅጣጫ እንደዚህ አይነት ፊልም መስራቱ አስፈላጊ ይመስለኛል። ይኼውላችሁ። ይህም ጀርመን ነው ብሎ።»
ጋዜጠኛ ያናም ትሁን ሙዚቀኛ ሳሚ ዴሉክስ ጥቁርና እና ጀመናዊ መሆናቸውን አሁን ድረስ ማብራራት ቢኖርባቸውም ከነሱ በፊት ከነበረው ጥቁር ትውልድ ጋር አይነፃጸርም። ቴውዶ-ቮይና ሚሻኤል እኢአ 1925 ዓም በበርሊን ከተማ ነው የተወለዱት። ሕፃን እያሉ ለአውደ ርዕይ ይቀርቡ ነበር። ቦታውም አሁን ድረስ የዱር እንስሳት እና አራዊት በሚጎበኝነት ስፍራ።«ይታያችሁ፤ ሰዎች ለእይታ ይቀርባሉ። እዛም አፍሪቃን ወክለው ቀሚስ ለብሰው በከበሮ፤ በሙዚቃ ፤ በጭፈራ ብቻ አፍሪቃውን የሚያደርጉትን እንዲያቀርቡ ይደረጋል። እነዚህ ነገሮች ግን ከበስተጀርባቸው ተመልከቱ እነዚህ መጤዎች ሀገራቸው እንዴት እንደሆነ ያሳያሉ በማለት ከዚህ ሀገር እንዳልሆንን ለመግለፅ የሚደረግ ነው።»
ጀርመን ውስጥ ሌሎች ነጭ የውጭ ሀገር መጤ ሰዎች ብዙም የቆዳ ቀለማቸው እንደ ጥቁር እንግዳ አያስብላቸውም። « ዘረኝነት ማለት በየጊዜው በቀኝ አክራሪዎች ከሚፈጸመው የኃይል ርምጃ በላይ የሆነና ከአስተሳሰብ ጋር የተያያዘ ነው። ብዙ ኃይል እና ጉልበት ያስጨርሳል። ሁል ጊዜ በእንደዚህ አይነት ጥያቄዎች መፈተን ቅር መሰኘትን ይፈጥራል። ለምሳሌ በአንድ ወቅት በአንድ የዜና ወኪል ለስራ ልምምድ አደርግ ነበር እና ጋዜጣዊ መግለጫ ልከታተል ሄድኩ ፤ እዛም «ከመስተንግዶ ነዎት አይደል፤ ቡና ያመጡልናል» አሉኝ። እኔ ደግሞ እረ አይደለሁም ስለጋዜጣዊ መግለጫው ልዘግብ ነው የመጣሁት አልኩኝ።
ዛሬ ያና ዶይቸቬለን ጨምሮ ለሁለት ጣቢያዎች የቴሌቪዥን ፕሮግራም አቅራቢ ናት። አፍሮ-ጀርመን በተሰኘው ፊልሟም ያነጋገረቻቸው ጥቁር ጀርመናውያን በጋራ ዘረኝነትን እንዴት መዋጋት እንደሚቻል፤ ሌሎች ምን አድርገው እንዳስቀየሟቸው እና ቢቀር ጥሩ ነው ብለው የሚያምኑትን ይገልጻሉ። በዚሁ ፊልም የተካፈለችው ኤስታ ዴንኮር ለምሳሌ ከርዳዳ ፀጉር ላላቸው ሰዎች የኦንላይን መፅሄት አዘጋጅታለች።« ከርዳዳ ፀጉር በማህበረሰባችን እንደ ቁንጅና አይታይም። ብዮንሴን እንደ ምሳሌ ብንወስድ፤ ጥቁር ናት፣ መድረክ ላይ ትቀርባለች። ጠንካራ ናት። ሁልጊዜ ግን ሉጫ ብሎንድ ዊግ እንዳጠለቀች ነው።»
ይህም የያና አንድ የፊልም አካል ነው።« ጀርመን ውስጥ 20 በመቶ የሚሆነው ህዝብ የውጭ ዝርያ ነው። ይህም ቁጥር ይጨምራል እንጂ አይቀንስም። ማቆም የማይቻለውን ነገር ለማቆም ከመሞከር እንዴት በጋራ መኖር እንችላለን ስለሚለው መወያየቱ ይሻላል። ወዴትም አንሄድም፤ ይህ ሀገራችን ነው። መቀበሉ ነው የሚሻለው።»
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ