ግጭት በኮንሶ
ረቡዕ፣ የካቲት 30 2008ለግጭቱ መንስዔ የሆነዉ የኮንሶ ህብረተሰብ ላለፉት አስርት ዓመታት በራሱ ልዩ ወረዳ ሲተዳደር የኖሮ፣ የፌዴራል እና የክልሉ መንግሥታት በወሰዱት እርምጃ ወረዳዉ ወደ ሴጌን አከባቢ ህዝቦች ዞን እንዲጠቀለል በመደረጉ ነዉ ሲሉ ነዋሪዎቹ ይናገራሉ። የኮንሶ ህብረተሰብ ወደ እዚህ ዞን መጠቃለሉን እንደማይቀበለዉ ነዋሪዎቹ በፁሁፍ ለመንግስት አቤቱታ ቢያቀርቡም መንግስት መልስ ባለመስጠቱ ሕዝቡ ተቀዉሞዉን እንዳሰማ እና መንግስት በላካቸዉ የፀጥታ ሃይላት በወሰዱት የሐይል እርምጃ ጉዳት ማድረሳቸዉን ነዋሪዎቹ ይናገራሉ።
የዞን ጥያቄዉ ከተነሳ ወዲህ ሰዎች ከስራ ገበታቸዉ መባረራቸዉን፣ የታሰሩ፣ የቆሰሉ እና የሞቱ ሰዎች እንዳሉ የኮንሶ ነዋሪ የሆኑት ዲኖቴ ኩስዬ ሼንቄሬ ለዶቼ ቬሌ ይናገራሉ። የወረዳዉ አመራርም እስር ላይ እንደሚገኙ ከተናገሩ በዋላ ህብረተሰቡ መንቀሳቀስ እንዳልቻለ ዲኖቴ ያብራራሉ። ኮንሶ በዓለም ቅርስነት ተመዝግባ የምትገኝ ሲሆን ዲኖቴም በዚሕ ልዩ ወረዳ ላለፉት 22 ዓመታት በአስጎብኚነት ሲሰሩ ቆይቶዋል። ይሁን እንጅ አሁን በተፈጠረዉ ግጭት ቱርዝሙ መታወኩን ገልጸዋል።
ጌሜቹ ገንፌ ሌላዉ የኮንሶ ነዋሪ ሲሆኑ ኮንሶ ህብረተሰብ ራሱን በራሱ ለማደረጀት ያነሳዉን ጥያቄ ለመንግስት አካል እንዲያቀርቡ ከተመረጡ የአካባቢዉ ነዋሪዎች አንዱ ናቸዉ። ኮንሶ ወደ ሌላ ዞን የተቀላቀለችዉ በጉልበት እንደሆነ ይናገራሉ። መንግስት መልሱን በፁሁፍ ለኮንሶ ህብረተሰብ እንድያቀርብ አቶ ጌሜቹ ቢጠይቁም መልሱ ሌላ እንደነበር አብራርተዋል።
ባለፈዉ ሳምንት በዶቼ ቬለ የፌስቡክ ደህረ ገፅ ላይ ይሄን ጉዳይ አስመልክቶ በተደረገዉ ዉይይት አብዛኞቹ መንግስት በሃይል ሳይሆን በመነጋገር ችግሩን እንዲፈታ አሳስቦዋል። ይሄንንም ለማድርግ ይላሉ አስተያየት ሰጭዎች መንግስት ህብረተሰቡን የሚጎዳ ፖሊስዎችን ማስተካከል አለበት።
መርጋ ዮናስ
ነጋሽ መሐመድ