ግሪክ ከዩሮ ሸርፍ እንዳትወጣ ማስጋቱ
እሑድ፣ ታኅሣሥ 26 2007ማስታወቂያ
የጀርመንዋ መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል እና የጀርመኑ የፊናንስ ሚኒስትር ዎልፍጋንግ ሾይብለ ግሪክ ከሸርፉ ተጠቃሚ ሃገራት መካከል ብትወጣ ጉዳት የለዉም ማለታቸው ተዘገበ። ይኽን በዘገባው ይፋ ያደረገው በጀርመንኛ ቋንቋ የሚታተመው «ሽፒግል» የተሰኘዉ መጽሔት ነው። የጀርመን የፊናንስ ሚኒስትር ግን በዘገባው ላይ ምንም አስተያየት አለመስጠቱ ተነግሯል። ግሪክ በቅርቡ የምታኪያሂደው አጠቃላይ ምርጫ ውጤት ሀገሪቱ በዩሮ ተጠቃሚነቷ ትቀጥል አትቀጥል የሚለውን ጥያቄ መልስ ያስገኛልም ተብሏል። ግሪክ ወደፊት ከዩሮ ሸርፍ ተጠቃሚ ሃገራት አባልነትዋ ብትወጣ እንኳን በአውሮጳ ኅብረት አባልነቷ የምትቆይበት መንገድ እየታሰበበት መሆኑን መጽሔቱ አትቷል። ግሪክን ከዩሮ ሸርፍ አባልነቷ እንድትወጣ ሊገፋት የሚችለው የደረሰባት የፊናንስ ቀውስ እና ያን ተከትሎ የምትከተለው የቁጠባ መርኅ እንደሆነም ተዘግቧል። ፖርቱጋል እና አየርላንድ ቀደም ሲል ከደረሰባቸዉ የፊናንስ ቀዉስ ማገገማቸዉም ተጠቅሶአል። ግሪክ ከዩሮ ሸርፍ ተጠቃሚ ሃገራት አባልነትዋ ብትወጣ በሀርፉ ተጠቃሚ ሃገራት ላይ ሊደርስ የሚችለው የፊናንስ ቀውስ የመነመነ ሊሆን እንደሚችል ተጠቅሷል።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
አዜብ ታደሰ