1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጋዜጠኛ ዳዊት ይስሃቅ ከእስር እንዲለቀቅ የተደረገ ጥሪ

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 9 2003

በትውልድ ኤርትራዊ በዜግነት ስዊድናዊ የሆነው ጋዜጠኛ ዳዊት ይስሀቅ አስመራ አቅራቢያ በሚገኝ ኤራይሮ እስር ቤት ከታሰረ ዘጠኝ ዓመት ሆነው። የአውሮፓ ህብረትና ሲውዲን ኤርትራ ላይ ጫና እንዲያደርጉ የተጠናከረ ጥሪ ቀርቧል።

https://p.dw.com/p/Phv5
ጋዜጠኛ ዳዊት ይስሀቅ

እ.ኤ.አ.መስከረም 2001። የዛሬ ዘጠኝ ዓመት አከባቢ። ኤርትራ ከጎረቤት ኢትዮዽያ ጋር የገጠመችው ጦርነት ባበቃ ማግስት ነው። በርካታ የጋዜጣ ባለቤቶች፤ አዘጋጆችና ጋዜጠኞች ለኢትዮዽያ ትሰልላችሁ ተብለው ታሰሩ። ከእነዚህም አንዱ በትውልድ ኤርትራዊ በዜግነት ሲውዲናዊ የሆነው ዳዊት ይስሀቅ ይገኝበታል። ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት ዳዊት ይስሀቅን ለማስለቀቅ የተደረገው ዘመቻ በእርግጥ የኤርትራን መንግስት አቋም የሚያስቀይር አልሆነም። በፈረንሳይ ስትራስቡርግ በሚካሄደው የአውሮፓ ፓርላማ አባላት ስብሰባ ላይ የአውሮፓ ህብረት ዳዊት ይስሀቅን የማስለቀቅ ግዴታ አለበት በሚል ወንድሙን ኢሳያስ ይስሀቅን ጨምሮ ሌሎች ቡድኖች ተሰባስበዋል። የሲዊዲን አንድ የጠበቆች ድርጅት፤ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ጠበቃ ፔርሲ ብራት ፤ ስዊዲንና የአውሮፓ ህብረት ዳዊት ይስሀቅ ከእስር ነጻ እንዲሆን የማድረግ ህጋዊ ግዴታ አለባቸው ይላሉ።

የብራት እና ፌይንሲልበር የጠበቆች ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ጠበቃ፤ ፔርሲ ብራት የአውሮፓ ህብረትና ሲውዲን የእስከአሁኑ ጸጥታ ያጠላበት አካሄዳቸውን አቁመው ጠንካራ እርምጃ መውሰድ አለባቸው ይላሉ።

ኢሳያስ ይስሀቅ የዳዊት ይስሀቅ ታናሽ ወንድም ናቸው። ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት የወንድማቸውን ነጻ መለቀቅ በተመለከተ በየጊዜው ድምጻቸውን ያሰማሉ። በኤርትራ መንግስት ለእስር የተዳረገው ወንድማቸው እንዲለቀቅ እየተካሄደ ያለው ግፊት እየተጠናከረ ቢሆንም የተገኘው ምላሽ ብዙም እንዳላረካቸው ገልጸዋል።

መሳይ መኮንን

ተክሌ የኋላ