ጀርመን- የገና ክብረ በአል እና የፕሪዝደንቱ ንግግር
እሑድ፣ ታኅሣሥ 15 2004
የጀርመኑ ፕሪዝደንት ክርስቲያን ቩልፍ በገና በአል መልካም ምኞት መግለጫቸዉ ማህብረሰቡ በነጻነት እንዲኖር በመቀራረብ ዲሞክራሲዉን እንዲያስጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል። ቩልፍ በመቀጠል አገራችን ዉጭ ዜጎች ላይ ለሚደረግ ጥላቻ፣ ለቀኝ አክራሪነት ቦታ የላትም ሲሉ እንዲህ ገልጸዋል።
«አገራችን ለሃይል ጥቃት፤ ዉጭ አገር ዜጎች ላይ ለሚደረግ ጥላቻ እና ለቀኝ አክራሪነት ቦታ የላትም። በቀኝ አክራሪዎች ለተገደሉት ቤተሰቦች እና ለጓደኞቻቸዉ ልባዊ ሃዘናችንን እና ክብራችን መግለጽ እንወዳለን። በዚህ ወንጀል ህይወታቸዉን ያጡት ሰዎች እንዴት እንደተገደሉ ወንጀለኞቹን ለምርመራ እና ለፍርድ ማቅረብ ብቻ ሳይሆን የወንጀለኞቹን ተባባሪዎች ተከታትሎ መያዝም ጭምር ይኖርብናል። በአገራችን ሁሉም ሰዉ በነጻነት እንዲኖር ለዲሞክራሲያችን ህልዉና፤ ጥንቃቄ እና ትብብር ስናደርግ ነዉ»
ዎልፍ ይህን ያሉት በጀርመን ለረጅም ግዜ ተደብቆ ሲንቀሳቀስ የቆየ አንድ የቀኝ አክራሪ ቡድን ሲራ ጉዳይን መሰረት አድርገዉ ነዉ። የሮማዉ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክት 16ኛ ሮማ ፔተርስ አደባባይ ላይ በገና በአል የሚያደርጉትን ባህላዊ የእንኳን አደረሳችሁ ንግግር አስር ሽህ አማኞች በተገኙበት አደረጉ። የሮማዉ ሊቃነ ጳጳሳት በአለማችን ሰላም እና ስምምነት እንዲነግስ ፣ እስራኤል እና ፍልስጤም ዳግም ድርድር እዲጀምሩ ጥሪ አቅርበዋል። በሶርያ የቀጠለዉ የሃይል እርምጃ እንዲያበቃም ጠይቀዋል። የጌታ መወለድ በኢራቅ እና በአፍጋኒስታን እርቅ እና ሰላምን እንዲያመጣ በሰሜን አፍሪቃ አገራት መልሶ መቋቋምያ አዲስ ሃይልን፣ በአፍሪቃ አገራት የፖለቲካ መረጋጋት እንዲሰፍን ሲሉ የገና በአል ምኞታቸዉን በዚህ መልኩ አስተላልፈዋል። ሊቃነ ጳጳሳቱ ከዚህ ቀደም ሲል በስድሳ አምስት የአለም ቋንቋዎች የእንኳን አደረሳችሁ መልክትም አስተላልፈዋል።
አዜብ ታደሰ
ማንተጋፍቶት ስለሽ