1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

«ደስታ»(ሪንደርፔስት)

ረቡዕ፣ ጥቅምት 10 2003

ፈንጣጣ፣ ከገጸ-ምድር የጠፋበት ብሥራት ፣ በ 1980(እ ጎ አ) ከተነገረ ወዲህ ለአያሌ ምዕተ-ዓመታት የቀንድ ከብቶች ዐቢይ መቅሠፍት ሆኖ የቆየው ደስታ(ሪንደርፔስት)ከምድራችን ሳይጠፋ እንዳልቀረ ባለፈው ሰሞን ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/PjQ7
ምስል Petr Pavlicek

በአማርኛ «ደስታ»፤ በእንግሊዝኛ ደግሞ በቀጥታ ከጀርመንኛው ተወስዶ «ሪንደርፔስት» የሚባለው የቀንድ እንስሳት አደገኛ በሽታ፣ በሰው ልጆች የረጅም ጊዜ ታሪክ ፤ በየዘመናቱ፤ በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ እንስሳትን መፍጀት ብቻ ሳይሆን ፣በሳቢያው፣ በተፈጠረ የምግብ እጥርት ሳቢያ ለብዙ ሰዎች የረሃብ ዕልቂት ሰበብ ሆኖ መቆየቱ የታወቀ ነው። ደስታ፣ የከብቶች በሽታ ኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የገባው፣ ቅኝ ግዛት ፈላጊ የኢጣልያ ወታደሮች፣ በ 1879 ዓ ም በቀይ ባህር በኩል ከህንድ ባስገቡአቸው

በበሽታው ተለክፈው በነበሩ ከብቶች ሳቢያ ነው። ይህ በሽታ በ 10 ዓመት ውስጥ እስከ ደቡብ አፍሪቃ ጫፍ ተዛምቶ 80 እስከ 90 ከመቶ፣ የአፍሪቃን ከብቶች ከመጨረሱም ኢትዮጵያ ውስጥ ፣ የከብቶችን ዕልቂት ተከትሎ በ 1880 እና 1884 ዓ ም መካከል ብቻ ፣ በረሃብ ሢሦው የኢትዮጵያ ህዝብ ህይወቱን አጥቷል። ይህን በሽታ ለማስወገድ አያሌ ዓመታት ቢወስድም በመጨረሻ ሊሳካ ስለቻለበት ሁኔታ ፣ በኢትዮጵያ የግብርና ሚንስቴር የአንስሳትና እጽዋት ጤናና ቁጥጥር አመራር ዋና ኀላፊ ዶ/ር በርሀ ገ/እግዚአብሔር--እንዲህ ይላሉ።

(ድምፅ)--------------

«ደስታ» ፣ የቀንድ ከብቶችን ፤ በአጠቃላይ የሚያመሠኩ እንስሳትን፣ ጉማሬዎችን ጭምር የሚጠናወተው በሽታ፣ ከገጸ ምድር ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መጥፋቱንም ሆነ መወገዱን በመጪው ግንቦት ወር ሳያረጋግጥ እንደማይቀር የተባበሩት መንግሥታት የምግብና የግብርና ድርጅት(FAO) ባለፈው ሐሙስ ማስታወቁ የሚታወስ ነው። በአንስሳት ህክምና ጠበብትም ሆኑ ምሁራን ዘንድ ፣ የ ደስታ በሽታ ከገጸ- ምድር ከእነአካቴው ስለመጥፋቱ የሚነገረው እስከምን ድረስ አስተማማኝነት ይኖረዋል?

ተክሌ የኋላ

መሳይ መኮንን