የ2015 አቀባበል በዓልና መልዕክቱ
ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 23 2007«ዘንድሮ የተስፋ አድማፅ ጨልሟል።ልባችን ቃላት በማይገልፁት እርምጃና በየዋሐን ሞት በሐዘን ተሞልቷል።ባሁኑ ወቅት የቀዝቃዛዉ ጦርነት ጣረ-መንፈስ እያደነን ነዉ።ከሁለተኛዉ ያዓለም ጦርነት ወዲሕ የዘንድሮን ያክል ስደተኛ፤ተፋናቃይና ጥገኝነት ጠያቂ ታይቶ አይታወቅም።»
ዓመቱ ለበጎ ይሁን ለመጥፎ አበቃ።ከሲድኒ እስከ ኒዮርክ፤ ከለንደን እስከ ቤጂንግ የሚገኘዉ ዓለም አዲስ በጎ ተስፋ እየተመኘ አዲስ ዓመት አለ።2015 -አንድ ነዉ ዛሬ።እንደየሐገሩ አቆጣጠር ትናንት እኩለ ሌት የበረቀዉን ዓመት ምክንያት በማድረግ የሐገራት መሪዎች፤የፖለቲካ ፓርቲና የድርጅት ተጠሪዎች፤የሐይማኖት አባቶች ለየሕዝባቸዉ የመልካም ምኞት መግለጫዎችን አስተላልፈዋል።በመግቢያችን እንዳልኩት የበዓሉን አከባበርና የመልዕክቱን ይዘት ባጭሩ እንቃኛለን።
የኒዮርክ በዓል አከባበር ነዉ ብዙ የተወራለት ታይምስ በተሰኘዉ አደባባይ ከአንድ ሚሊዮን የሚበልጥ ሕዝብ ርችቱን ሲለኩስ፤ ሲተኩስ፤ ሲጠጣ፤ ሲጨፍር ነዉ ያደረዉ።
ለቻይናዉ ሻንግሐይ ከተማ ጥሩ ሌት አልነበረም።አንዱ ሸረኛ ከፎቅ ላይ ዶላር የሚመስል ወረቀት ለበዓል በተሰበሰበዉ መሐል በትኖ ሕዝቡን ሲያሻማ ሰላሳ ስድስር ሰዎች ተረጋግጠዉ ሞቱ።ፊሊፒንስም አንድ የድሆች መንደር በሳት ጋይቶ ብዙ ሰዎች ሞተዋል።ፓሪስ -ለበዓሉ ፌስታ ሻዘ ኤልዜ የተሰኘዉን አዉራ መንገድ ለመኪኖች ዝግ ሆኖ ነዉ ያደረዉ።ያም ሆኖ ከአዉሮጳ ከተሞች በመብራት በማሸብረቅ፤በቅዝቃዜም ሞስኮን የተስተካከለ የለም። ከደቡብ አሜሪካኞች ደግሞ ዓመቱን የብራዚሎችን ያክል በደማቅ ድግሥ-ፈንጠዝያ የተቀበለዉ የለም ነዉ-የሚባለዉ።በነገራችን ላይ ባለፈዉ ጥቅምት ማብቂያ በድጋሚ የተመረጡት የብራዚሏ ፕሬዝዳንት ዲልማ ሩሴፍ ሁለተኛ ዘመነ-ሥልጣናቸዉን ዛሬ ነዉ የጀመሩት።ሌሊቱን ኳስ፤ ዳስ፤ ፌስታ የሚወደዉ የብራዚል ሕዝብ በተለይ ኮፓካባና የተሰኘዉን የባሕር ዳርቻ አሸዋን በጭፈራ ሲያረባየዉ ነዉ-ያደረዉ።
በጭፈራ-ዳንኪራ፤ በርችት ተኩስ ግርግሩ መሐል በተለይ ለካቶሊክ እምነት ተከታዩ የሮማ ካቶሊካዊቷ ቤተ-ክርስቲያን ርዕሠ-ሊቀነ ጳጳሳት ፍራንሲስ ቡራኬ፤ ፀሎት፤መልዕክት ሲንቆረቆር ነበር።ሌሎቹስ ምን አሉ ይሆን። ምን ለማድረግስ ተዘጋጅተዋል።
ሃና ደምሴ
መክብብ ሸዋ
ይልማ ኃይላሚካኤል
ነጋሽ መሐመድ