የ SMS ቁጥጥር በኬንያ
ሰኞ፣ ጥቅምት 19 2005እኢአ 2007 ዓም በኬንያ በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በተለያዩ የፓርቲ አባላት እና ጎሳዎች መካከል በተነሳ አመፅ ከ 1000 በላይ ሰዎች ህይወት መጥፋቱ እና በመቶ ሺ የሚቆጠሩ ሰዎች መሰደዳቸው የሚታወስ ነው። በመጪው መጋቢት ወር በኬንያ ቀጣይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ይካሄዳል። በአሁኑ ምርጫም ያለፈው አይነት አመፅ ተነስቶ ግድያ እንዳይፈፀም በሀገሪቱ ትልቅ ስጋት አለ። አንዳንድ ተንታኞች እንደሚሉት ባለፈው ምርጫ ብጥብጡን ያፋፋመው ጥላቻ የተሞላ አጫጭር የፁሁፍ መልዕክት ነው። ይህን ለማስቀረትም ቅድመ ምርመራ እንዲካሄድ መወሰኑን የኬንያ የመገናኛ ብዙኻን ገልፀዋል።
የኬንያ የመገናኛ ዘዴዎች ጉዳይ ምክትል ዳሬክተር ክርስቶፈር ከሚ አዲሱ የSMS ቁጥጥር መመሪያ የሚኖረውን አስተዋፅዎ ያብራራሉ።
« የመመሪያዎቹ አላማ በመሰረቱ አንዳንድ ሰዎች በተለይም ፖለቲከኞች የምርጫ ዘመቻቸውን በሚያካሂዱበት ወቅት በሞባይል የሚሰዱት መልዕክት ይዘት የሃገሪቱን ህገ መንግስቱን የማይፃረሩ እንደሆኑ ሰዎች ያለ ፍርሃት ህጉን የሚጥሱበትን ሁኔታ ለመቀነስ ነው»
የምርጫ ዘመቻ መልዕክቶችን የሚቆጣጠረው የመገናኛ ዘዴዎች ጉዳይ የሆነ አንድ የመንግስት መስሪያ ቤት ነው። ፖለቲከኞች ለህዝቡ ለመላክ የሚፈልጉትን መልዕክት 48 ሰዓት አስቀድመው እንዲያስረክቡ አዲሱ መመሪያ ያሳስባል። የሀገሪቱ ዕለታዊ ጋዜጣ « DAILY NATION» እንዳስታወቀው መልዕክቱ በእንግሊዘኛ እና በሱሀሊኛ ቋንቋ ብቻ መሆን አለበት ። መልዕክቱ የሚደርሳቸው ሰዎች ደግሞ አስቀድመው ይህንን አገልግሎት የተኮናተሩ ናቸው። ህዝቡ ይህንን የመልዕክት ይዘት ቅድመ ቁጥጥር እንዴት ተቀበለው? አሁንም ክርስቶፈር ከሚ « በአጠቃላይ ጥሩ ምላሽ ነው የነበረው። በዚህ መመሪያ ላይ አስተያየት የሰጡ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሙሉ ይህንን አሰራር በቀና ተቀብለውታል። ምክንያቱም ሁሉም ኬንያዊያን ምርጫውን ተከትሎ በ2007 እና በ2008 የተከሰተውን በድጋሚ ማየት አይፈልጉም።»
ፖሊስ ህግ የሚጥሱትን በቁጥጥር ስር ለማዋል አስፈላጊውን መሳሪያ እየቀረበለት መሆኑን ክርስቶፈር ከሚ ከዶይቸ ቬለ ገልፀዋል። አዲሱ መመሪያ በርግጥ የምርጫ ዘመቻው ከቁጥጥር ውጪ እንዳይሆን ሲባል የታሰበ ነው፤ ወይንስ ሀሳብን በነፃ የመግለፁን መብት መመሪያው ይፃረራል? ክርስቶፈር ከሚ፤ « መመሪያው የታቀደበት ዋና አላማ በምርጫ ዘመቻው ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ ሰዎች አላማቸውን ሳያሳንስ የሚተገብሩበት መንገድ ይሆናል። የህዝቡን ወዳጅነት እና ደህንነት እንደተጠበቀ ሆኖ።»
ለፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የቀረቡት ፤ ራይላ ኦዲንጋ፣ ካሎንዞ ሙስዮካ፣ ኡሁሩ ኩንያታ እና ዊልያም ሩቶ ሁሉም ለደጋፊዎቻቸው ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ በአጭር የፁሁፍ መልዕክት ወይንም SMS ተደራሽ ያደርጋሉ። በርግጥ መመሪያው ለምርጫ ዘመቻው የነበረውን ሚና ግን ከምርጫው በኋላ የምናየው ይሆናል።
ልደት አበበ
ሒሩት መለሰ