የፕረስና የጋዜጠኞች ይዞታ በ 2012 ጎ.ዓመት
ዓርብ፣ የካቲት 8 2005፤ በእነዚህ እሴቶች ላይ ያተኮረ መርኅ መዘርጋት የሚፈልጉ አይመስሉም።ለጋዜጠኞች መብት መጠበቅ አጥብቆ እንደሚታገል የሚነገርለት CPJ በየጊዜው እንደሚያደርገው ሁሉ፤ ዘንድሮም ፣ የፕረስ ነጻነትንና የጋዜጠኞችን ይዞታ በተመለከተ በህትመት መልክ ያቀረበውን መጽሐፍ ትናንት ይፋ አድርጓል።
2012 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት ለጋዜጠኞች ጨፍጋጋ እንጂ ብሩኅ ዘመን አልነበረም። የተገደሉት ጋዜጠኞችም መጠን ከሃቻምናው ንሮ ነው የተገኘው። የምሥራቅ አፍሪቃ ጉዳዮች ተከታታይና የ CPJ አማካሪ ቶም ሮደስ ስለዚህ ጉዳይ ምን ይላሉ?
«CPJ በያመቱ «በፕረስ ላይ የሚሠነዘር ጥቃት» በሚል ርእስ መጽሐፍ እያተመ ያቀርባል። የዚህ ዓመት በተለይ አስደንጋጭ ነው። እኔ ይበልጥ የምመለከተው የአፍሪቃውን ቢሆንም በዓለም አቀፍ ደረጃ ስናየው ከዚህ ቀደም ታይቶ ባልታወቀ ሁኔታ በዛ ያሉ ጋዜጠኞች ተገድለዋል። ቁጥራቸው ከፍ ያለም ተይዘው ታሥረዋል። እዚህ ላይ ማውሳት የምፈልገው አፍሪቃ የዚህ ሂደት ምልክት እንደማይታይበት ነው። ዘንድሮ ከብርቱ ወቀሳ ለማምለጥ ችሏል። »
ይህን ሲሉ ምንድን ነው ለማስጨበጥ የፈለጉት፦ በአፍሪቃ ሁኔታዎች ተሻሽለዋል ነው የሚሉን፦ የአፍሪቃውን የፕረስ ነጻነት ይዞታ እርስዎ እንዴት ነው የሚገመግሙት?
«እርግጥ አጠቃሎ ለመናገር ያስቸግራል። አፍሪቃ ሰፊና የተለያዩ ሁኔታዎች የሚንፀባረቁበት ክፍለ ዓለም ነው።አገሮች ሁሉ የተለያየ ሁኔታ ነው የሚንጸባረቅባቸው።
እርግጥ በአፍሪቃው ቀንድና በምሥራቃዊው የክፍለ ዓለሙ ማዕዘን፣ የተባባሰ ሁኔታ መኖሩን ነው የምንገነዘበው። ለምሳሌ የሶማልያን ይዞታ ብንመለከት፣ ዘንድሮ በዛ ያሉ ጋዜጠኞች መገደላቸውን አስተውለናል። ከ 1983 ዓ ም ወዲህ ብዛታቸው ወደር የለውም። በአሥራት የሚማቅቁትም፤ ብዙዎች ናቸው። ኤርትራ ነበረች፤ ጋዜጠኞችን ፤ በዘፈቀደ ይዞ በማሠር መጥፊ ስም ይዛ የቆየች። 28 ያህል ሳይሆኑ አይቀሩም ወህኒ የወረዱት። እርሷም ብቻ ሳትሆን ፤ ጎረቤቷም፣ ያሳዝናል ፣ ኢትዮጵያም ሁለተኛውን ሥፍራ ይዛለች። አምና 6 ጋዜጠኞችን ወደ ወህኒ ወርውራለች። አሁን በጠቅላላ ቁጥራቸው ሰባት ደርሷል።»
በዓለማችን ፤ የዴሞክራሲ መለኪያ የሆነው የፕረስ ነጻነት እንዲጠበቅ፤ CPJ ም ሆነ ሌሎችየፕረስ ነጻነትና የሰብአዊ መብት ጠበቆች ይወተውታሉ። በኢንዱስትሪ የበለጸጉት ዴሞክራቲክ አገሮችም፤ ስለዚህ ጉዳይ አስፈላጊነት በየጊዜው ሲናገሩ ይሰማል። ግን ቋቱ ጠብ ሲል አይታይም። እናንተን ታዲያ፤ ጉዳዩ፣ እስከምን ድረስ ነው የሚያስቆጣችሁ፤ የሚያናድዳችሁ፤ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብስ ምን ማድረግ ይጠቅበታል ይላሉ?
«አመሠግንኻለሁ፤ በጣም ጥሩ ጥያቄ ነው ከአንጀት ለመናገር ይህ ያለውን የተመጻዳቂነት ይዞታ ነው የሚያንጸባርቀው በአፍሪቃ ዲሞክራሲ እንዲገነባ፣ የጽሑፍና የንግግር ነጻነት እንዲሠፍን፤በአንደበታቸው የሚናገሩትን መንግሥታት ተመጻዳቂነት ነው የሚያሳየው።
በሌላ በኩልም፤ አሁንም ቢሆን የፕረስ ነጻነትን የማይፈቅዱ አገዛዞችን ጭምር ይደግፋሉ። ለምሳሌ በቅርቡ በሶማልያ አንድ ጋዜጠኛ ቃለ-ምልልስ በማድረጉ ብቻ ነበረ የተያዘው። የብሪታንያና የዩናይትድ እስቴትስ ውጭ ጉዳይ ሚንስትሮች፣ የ ተ መ ድ ዋና ጸሐፊ ባን ኪ ሙን--እነዚህ ሁሉ አጥብቀው ሲቃወሙ ይሰማል። ግን ከዚያ አልፈው አይሄዱም።
እንደሚመስለኝ፤ ለአኛ ለፕረስ ነጻነት ጠበቆች አስቸጋሪዎች ከሆኑብን ጉዳዮች አንዱ ይህ ዓይነቱ ነው። መንግሥታት ለሚሠሩት ተጠያቂነት እንደሌለባቸው እስካወቁ ድረስ፣ በዚያው መሥመር ነው የሚያደርጉትን የሚቀጥሉበት። እናም ሂስ የሚሰነዝሩ ወገኖችን ድምፅ ለማፈን መጣሩን ይገፉበታል።»
ተክሌ የኋላ
ሸዋዬ ለገሰ
ነጋሽ መሐመድ