የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ብይን
ዓርብ፣ ሐምሌ 6 2004
የኢትዮጵያ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በአሸባሪነት የተከሰሱትን ሃያ-አራት ጋዜጠኞችና ተቃዋሚ ፖለቲከኞችን ከሰባት ዓመት እስከ እድሜ ልክ በሚደርስ እስራት ቀጣ።ዛሬ አዲስ አበባ ያስቻለዉ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተቃዋሚዉን የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ (አንድነት ባጭሩ) ከፍተኛ ባለሥልጣን አንዱ ዓለም አራጌን የእድሜ ልክ እስራት በይኖባቸዋል።ጋዜጠኛና ፀሀፊ እስክንድር ነጋ ደግሞ በአስራ-ስምንት ዓመት እስራት ተቀጥቷል።ሌሎቹ ተከሳሶች ከሰባት ዓመት እስከ እድሜ ልክ የሚደርስ የእስራት ቅጣት ተበይኖባቸዋል።የፍርድ ቤቱን ዉሳኔ የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚዎችና የተለያዩ ዓለም አቀፍ የመብት ተሟጋች ድርጅቶች አጥብቀዉ አዉግዘዉታል።
ተቃዋሚዉ የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትሕ ፓሪቲ ቃል አቀባይ ዶክተር ሐይሉ አርአያ ፍርድ ቤቱን «አሸባሪ» ሲሉት፥ የፓርቲዉ አባልና ብቸኛዉ ተቃዋሚ የምክር ቤት አባል አቶ ግርማ ሠይፉ ደግሞ የተፈረደባቸዉ ሰዎች ያጠፉት ነገር የለም ብለዋል።
ከዉጪ ሲፒ ጄ በሚል ምሕፃረ ቃል የሚጠራዉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት የኢትዮጵያ መንግሥት «አሸባሪነትን መዋጋትን ሰላማዊ ድምፆችን ለማፈን እየተጠቀመበት ነዉ» በማለት አዉግዞታል።የዓለም አቀፉ የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት የሑዩማን ራትስ ዋች የአፍሪቃ ጉዳይ አጥኚ ቤን ሮዉሌንስ በበኩላቸዉ ፍርዱን «አናዳጅ» ብለዉታል።
«አልገረመኝም።ምክንያቱም ከኢትዮጵያ ፍርድ ቤት እንዲሕ አይነት ዉጤት እንጠብቅ ነበርና። ይሁንና በርግጥ በጣም አዝኛለሁ።ምክንያቱም ፍርሐትሕ ሲረጋገጥ ሁሌም አሳዛኝ ነዉና።በተጨማሪም በጣም ተናድጃለሁ።ምክንያቱም የኢትዮጵያን የሠብአዊ መብት ይዞታ እንደሚከታተሉት እንደሌሎች ብዙ ሰዎች ሁሉ፥ይሕ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ኢትዮጵያ ዉስጥ ያየነዉ፥ ሥርዓቱ የሚፈፅመዉ እመቃና የትኛዉንም አይነት የመናገር ነፃነት አለመታገሱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየባሰ ለመምጣቱ የመጨረሻዉ ማረጋገጪያ በመሆኑ።እና ለኢትዮጵያ የፕረስ ነፃነትና ለመናገር ነፃነት አሳዛኝ ቀን ነዉ።»
ፍርድ ቤቱ ዛሬ እስራት ከፈረደባቸዉ ሃያ-አራት ተከሳሾች አስራ-ስድስቱ ሐገር ዉስጥ የሉም። ፖለቲከኛ አንዱ ዓለም አራጌና ጋዜጠኛ እስክድር ነጋን ጨምሮ ሌሎቹ ተከሳሾች ግን ካለፈዉ መስከረም ጀምሮ እስር ቤት ናቸዉ።የኢትዮጵያ መንግሥት አዲስ ባፀደቀዉ የፀረ-ሽብር ሕግ ጋዜጠኞች ሲፈረድባቸዉ በሰባት ወራት ዉስጥ የዛሬዉ ሰወስተኛዉ ነዉ።
ታደሰ እንግዳው
ሂሩት መለሰ
ሸዋዬ ለገሠ