የፉኩሺማ አንደኛ አመት መታሰቢያ
ዓርብ፣ መጋቢት 7 2004በፉኩሺማ በደረሰው የመሬት ነውፅ እና ሱናሚ በሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወት አልፏል። በጃፓን የታየው የተፈጥሮ አደጋ አለም አቀፉን ህብረተሰብ፣ አሳዝኗል፣ መለስ ብሎም እንዲያስብ አድርጓል።
ጃፓን ከአንድ ዓመት በፊት በመሬት ነውፅና ማዕበል ሳቢያ የሞቱትንና የደረሱበት ሳይታወቅ የጠፉትን ከ 19 ሺህ የሚበልጡ የተፈጥሮ ቁጣ ሰለባዎች ባለፈው ሳምንት አስባለች። ዕለቱን ምክንያት በማድረግ በቶኪዮና በሌሎች ከተሞች በአደባባይ የተሰለፉ የሐገሪቱ ዜጎች የአቶም ሃይል ጣቢያዎች በሙሉ እንዲዘጉ ጠይቀዋል። እዚህ ጀርመንም የጃፓኑን መታሰቢያ ዕለት ምክንያት በማድረግ በርካታ የተፈጥሮ ተንከባካቢዎች ጸር-ኑክሌያር ተቃውሞ አሰምተዋል። የበርሊን ከተማ ነዋሪ የሆነው -ፓትሪክ፤ የፉኩሺማን አስከፊ አደጋ እንደ በርካታ ጀርመናዊያን በመገናኛ ብዙኃን ተከታትሏል። ይሁንና ዘገባው ለሱ በቂ አልነበረም። « ማለት አሁን 2ኛ እና 3ኛው የፉኩሺማ የአቶም ሃይል ጣቢያዎች በጠቅላላው የፍንዳታ ድምፅ እንዳሰሙ አውቃለሁ። ግን ይህ በዜና አልቀረበም። ምክንያቱም የአውሮፓ ትኩረት ሌላ ነገር ላይ ነበረና!»
በርግጥ አውሮፓን በአሁኑ ሰዓት የሚያሳስባት እንደ ግሪክ የፋይናንስ ቀውስ የመሳሰሉ ጉዳዮች አሉ። ይሁንና የፉኩሽማ አደጋ ትልቅ የመነጋገሪያ ርዕስ ሆኖ ሰንብቷል። የጃፓን አሳዛኝ ጥፋት ጀርመን ነገ በኔ ነው ብላ ርዕሷ አደረገች፤ ምክንያቱም እንደ ጃፓን ጀርመንም የኤሌክትሪክ ኃይል የምታመነጭበት በርካታ የአቶም ጣቢያዎች አሏት።
ይህም ጉዳይ ለብዙ አመታት ርዕስ ሆኖ ሁሉም ፖለቲከኞች ሲወያዩበት ቆይተዋል። ካርል ቤር -ከአረንጓዴዎቹ ፓርቲ የወጣቶች ክንፍ ነው።
« በርግጥ ብዙ በጎ ነው ብዬ ስለፉኩሺማ መናገር አልችልም ግን ከዚህ አንድ ልንማር የምንችለው ነገር ካለ፤ የኒኩሌር የሀይል ምንጭ ያህል አደገኛ እንደሆነ እና በአገልግሎት ላይ መዋል እንደሌለበት ነው።»
የጀርመን መንግስት እኢአ በ2000 ዓ ም እስከ ከ2022 ድረስ በአጠቃላይ የአቶም ሃይል ጣቢያዎቹን እንደሚዘጋ አሳውቋል። በርግጥ ጀርመን በ2022 የአቶም ኃይል ታቆም ይሆን? ፍሬአ ቴን በበርሊን አደባባይ ወተው ጸር-ኑክሌያር ተቃውሞ ካሰሙት ውስጥ አንዷ ነች።
« ከትምህርት ቤቴ እና የክፍሌ ልጆች፤ ከዚህ ቀደም ጨርሶ በፖለቲካ ውስጥ የሌሉበት ወይንም የተለያየ የፖለቲካ አቋም የነበራቸው በሙሉ ተሰብስበን አንድ ነጥብ ላይ ሁላችንም ተስማምተን አንድ የሆነ ስሜት ፈጠርን። »
ከፉኩሺማ አደጋ በኋላ ጀርመን ሰባት ያረጁ የአቶም ሃይል ጣቢያዎቿ ተዘግተው እንዲቆዩ ወስናለች። የበለጠ የፉኩሺማ አንደኛ አመት መታሰቢያን በተመለከተ የቶኪዮ ዘጋቢያችን ወሰንሰገድ መርሻ ያጫወተን አለ። ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሐመድ