1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የፈረንሳይ የጦር ሠፈር በፋርስ ባሕረ-ሠላጤ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 18 2001

ባካባቢዉ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ለመሳተፍ አሰፍስፈዉ ይጠብቁ የነበሩት ፈረንሳዮች አቡዳቢ ላይ የሚሽቱን እንዲያደርጉ የተባበሩት አረብ ኤምሬት-አሚሮች ፈጥነዉ የፈቀዱትም በዚሕ ምክንያት ነዉ

https://p.dw.com/p/HxfI
የፈረሳዩ ፕሬዝዳንትና የተአኤ ም/ጠሚምስል AP

ፈረንሳይ በፋርስ ባሕረ-ሠላጤ አካባቢ የመጀመሪያዋ የሆነዉን ቋሚ የጦር ሠፈር ዛሬ የተባበሩት አረብ ኤምሬት ዉስጥ በይፋ ከፈተች።በነዳጅ ሐብት በበለፀገዉና ከፍተኛ ሸቀጥ በሚመላለስበት ሥልታዊዉ አካባቢ የተመሠረተዉን የጦር ሠፈር መርቀዉ የከፈቱት የፈረንሳዩ ፕሬዝዳት ኒኮላይ ሳርኮዚ ናቸዉ።የጦሩ ተልዕኮ «ድጋፍ ሰጪ» የሚል ሥም ቢሰጠዉም አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ፈጥኖ የመንቀሳስና የመዝመት አቅምና ሐላፊነት አለዉ።አራት መቶ ሐምሳ ወታደሮች የሰፈሩበት የጦር ሰፈር ፈረንሳይ ማዕከላዊ አፍሪቃና ጅቡቲ ካሏት የጦር ሰፈሮች ጋር ሰወስተኛዉ መሆኑ ነዉ።ካርሽተን ኩሕንቶፕ የዘገበዉን ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

ፈረንሳዮች በባሕረ-ሠላጤዉ አካባቢ ምጣኔ ሐብታዊ፥ፖለቲካዊና ወታደራዊ እንቅስቃሴ መሳተፉን አጥብቀዉ ይመኙታል።የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ደግሞ fለፈረንሳዮች ምኞት ስኬት ክንዳቸዉን ዘርግተዉ ተቀበሏቸዉ።የባሕረ-ሥላጤዉ አካባቢ ነገሥታት በተለይ እንደ አዉሮጳዉያኑ አቆጣጠር በ2003 ኢራቅ ከተወረረች ወዲሕ የዩናይትድ ስቴትስ ብቻ ጥገኛ መሆኑን እየቀነሱ ከሌሎች ሐያላን ጋር መወዳጀቱን እንደ መሠረታዊ መርሕ እየተከተሉት ነዉ።

ዩናይትድ ስቴትስ ኢራን ለረጅም ጊዜ መክተዉ የያዙትን የቀድሞዉን የኢራቅ ፕሬዝዳት ሳዳም ሁሴንን ካስወገደች ወዲሕ የባሕረ-ሠላጤዉ አካባቢ የሐይል-አሰላለፍ ተቀይሮ ኢራን ያለጠንካራ ተቀናቃኝ ያካባቢዉ ሐይል ሆናለች።ይሕን ነገስታቱ አይፈልጉትም።የፕሬዝዳት ቡሽ መስተዳድር ይከተል የነበረዉ መርሕ ደግሞ የሐብታሞቹን ግን የትናንሾቹን ሐገራት ነገስታት ከተጨማሪ ሥጋት፥ ሌላ አማራጭ ከመፈለግ ብልሐት ነዉ-የዶላቸዉ።

ባካባቢዉ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ለመሳተፍ አሰፍስፈዉ ይጠብቁ የነበሩት ፈረንሳዮች አቡዳቢ ላይ የሚሽቱን እንዲያደርጉ የተባበሩት አረብ ኤምሬት-አሚሮች ፈጥነዉ የፈቀዱትም በዚሕ ምክንያት ነዉ።የአቡዳቢዉ የወታደራዊ ጉዳይ አጥኚ ኤሚል ሆካያም እንደሚሉት አቡዳቢ ብቻ ሳይትሆን ሌሎች የአካባቢዉ ሐገራትም የሚከተሉት ሥልት ተመሳሳይ ነዉ።

«የባሕረ-ሥላጤ አካባቢ ሐገራት የጦር መሳሪያ ክምችትና የጦር ሐይል ብዛት ፀጥታቸዉን ለማስጠበቅ እንደማይበጃቸዉ ይገነዘባሉ።ፀጥታቸዉን የሚጠበቀዉ የአለም አቀፉ አካል በመሆን ነዉ። ይሕን በማወቃቸዉም በአለም አቀፍ ጉዳዮች ከፍተኛ ሚና ለሚጫወቱት ሐይላት ሁሉ ያላቸዉን እየፈቀዱ ነዉ።ለዚሕም ነዉ የፈረንሳዩ እዉቅ ቤተ-መዘክር-ደ ለቩር እዚሕ የገባዉ፥ለዚሕም ነዉ የፈረንሳይ የባሕር ሐይል እዚያሕ የሠፈረዉ።ለዚሕም ነዉ-የዋሽንግተኑ ጆርጅታዉን ዩኒቨርስቲን ቀጠር የምናየዉ።ለዚሕም ነዉ ዩናይትድ ስቴትስ እዚሕ የመጣችዉ።»

ሆካያም እንዲሕ አይነቱን ሥልት-የብልሆች ይሉታል።

«በተቻለ መጠን ብዙ-ግን በጣም ሐይለኛ ወዳጆች እንዲኖራቸዉ ይፈልጋሉ።ይሕ ደግሞ በጣም ብልሐት የተሞላበት ሥልት ነዉ።እራሳቸዉን በአለም አቀፉ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሐብታዊ መዋቅር ዉስጥ እያሳተፉ ነዉ።»

በወታደራዊ ጉዳዮች አጥኚዉ እምነት የአረቦቹ-ነገስታት ፀጥታቸዉን የሐያላኑ ፀጥታ አካል ማድረግ ነዉ-አላማቸዉ።ኢራን ባንፃሩ የምዕራብ ሐገራት ጦር በአካባቢዉ መስፈሩን አጥፈቅደዉም።

Sarkozy weiht neuen Militärstützpunkt in Abu Dhabi ein
ራፋኤል-ጄትምስል AP

«የባሕረ-ሠላጤዉ መንግሥታት የአካባቢዉን ፀጥታ አለም አቀፋዊ ለማድረግ ይፈልጋሉ።ኢራን በተቃራኒዉ አካባቢያዊ ለማድረግ ነዉ-የምትሻዉ።ይሕ ማለት ኢራን የዉጪ ሐይላት በሙሉ ካካባቢዉ እንዲወጡ ትጠይቃለች።ኢራን ይህን የምትጠይቀዉ ባካቢዉ የበላይነትን ሥለሚያስገኝላት ነዉ።የባሕረ-ሠላጤዉ መንግሥታት ከማንጋር መወዳጀት እንዳለባቸዉ የመወሰን መብት አላቸዉ።ኢራንም ወረራን የሚቃወም መርሕ ሊኖራት ይገባል።ይሕ እንዴት ገቢር ይሆናል? በርካታ ሁኔታዎችን የሚያጣቅስ ነዉ።ሁኔታዎቹ ደግሞ ከባርረ-ሠላጤዉ አካባቢ ጋር ብቻ የተያያዙ አይደሉም።»

ፕሬዝዳት ሳርኮዚ በአቡዳቢ ቆይታቸዉ ራፈኤል የተሰኘዉን የሐገራቸዉ የጦር ጄት ለመሸጥ ከአስተናጋጆቻቸዉ ጋር ይዋዋላሉ።አረብ ኤሚሬቶች ከዚሕ ቀደም ከፈረንሳይ 60 ሚራጅ ጄትና አራት-መቶ ታንክ ገዝታለች።

ካርሽተን ኩሕንቶፕ /ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ፣

►◄