የጋዜጠኛ ታደሰ እንግዳዉ መታሰቢያ
ሰኞ፣ ጥር 29 2009ማስታወቂያ
ሐምሌ 8፤ 2004 ዓ.ም በመኪና አደጋ በሞት የተለየን ጋዜጠኛ ታደሰ እንግዳዉ ዛሬ ጀርመን ቦን ከተማ በሚገኘዉ የዶቼ ቬለ ራድዮ ጣብያ ሕንጻ ዉስጥ ቋሚ የማስታወሻ ሰሌዳ ታስቦ ዋለ። ዶይቼ ቬለ በዋና መሥሪያ ቤቱ ሕንጻ መግብያ ላይ አዲስ ባሰራዉ ሰሌዳ ላይ ጋዜጠኛ ታደሰ እንግዳዉን ጨምሮ ስራ ላይ ሳሉ በአደጋ አልያም በአሸባሪዎች የተገደሉ ሌሎች ሰባት የዶይቼ ቬለ ጋዜቸኞች ስም ሠፍሯል። ከ30 በላይ ቋንቋ በሚሰራጭበት ዋና ጣብያ ሕንፃ ላይ የተሰራዉ መታሰቢያ በይፋ በተመረቀበት ሥርዓት ላይ በርካታ ጋዜጠኞች፤ የጣቢያዉ ሠራተኞች ባለሥልጣንት ተገኝተዋል። የማስታወሻ ሰሌዳዉን መርቀዉ የከፈቱት የዶይቸ ቬለ ዋና ስራ አስኪያጅ ፔተር ሊምቡርግ ጋዜጠኞች ሥራቸዉን በትጋት ሲሰሩ የነበሩ ወንድሞቻቸን ዘላለም ይታወሳሉ ሲሉ ተናግረዋል። የሕሊና ፀሎትም ተደርጎአል። ከ 1996 ዓ.ም ጀምሮ ለዶይቼ ቬለ የአማርኛዉ አገልግሎት ሲዘግብ የቆየዉ ባልደረባችን ጋዜጠኛ ታደሰ እንግዳዉ ባለትዳርና የሦስት ወንዶች ልጆች አባት ነበር።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሃመድ