የጉድላክ ጆናታን የጀርመን ጉብኝት
ሐሙስ፣ ሚያዝያ 11 2004የጉዟቸው አላማ ሐገራቸው ከጀርመን ጋ ያላትን ግንኙነት ለማጠናከር ነው። ከ30 አመታት በኋላ ናይጀሪያን የጎበኙት የመጀመሪያዋ የጀርመን መራሒተ መንግስት አንጌላ መርክል ናይጄሪያን ከጎበኙ እንኳን ገና አመት አልሞላቸውም። ሁለቱም አገራት ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ የትብብርራቸውን ማጠናከር ይሻሉ።
ከ 150 ሚሊዮን ህዝብ በላይ በምዕራብ አፍሪቃዊቷ አገር - ናይጄሪያ ይኖራል። በህዝብ ብዛት ከአፍሪቃ የመጀመሪያዋ ናት። በዛ ላይ አገሪቷ ያላት የተፈጥሮ ሀብት ጀርመን ትኩረቷን ይበልጥ ናይጄሪያ ላይ እንድትጥል አድርጎታል። « በዚህ ምክንያት ናይጄሪያን እንደ አንድ አፍሪቃዊ አጋር ይበልጥ ትኩረት የምትሰጣት ትሆናለች። ምክንያቱም ከደቡብ አፍሪቃ ቀጥሎ ጠንካራ ምጣኔ ሀብታዊ ኃይል ናት። በዲሞክራሲ አካሄዱም ቢሆን ናይጄሪያ ትንሽም ቢሆን የተረጋጋች አገር ናት።»
ይላሉ የአፍሪቃን ጉዳይ የሚያቁት የጀርመን ፖለቲከኛ ሐርትቪግ ፊሸር፤በጀርመን የህዝብ እንደራሴ ም/ቤት የክርስቲያን ዲሚክራቲክ እና ሶሻል ህብረት ተጠሪ ናቸው። እናም አሉ ፊሸር፤ ናይጄሪያውያን ጀርመኖች የሚጎድላቸው አሏቸው። ይኼውም ናይጄሪያ ከ አስሩ የአለም ነ ዳጅ አምራቶች ተርታ ትሰለፋለች። ናይጄሪያ በቀን ሁለት ሚሊዮን በርሚል ነዳጅ ታመርታለች። በተለይ በደቡባዊው ኒጀር ዴልታ! በነዳጅ ዘይት ምርት ናይጄሪያ ከአለም የ7ኛነትን ደረጃ ይዛለች። የነዳጅ ዘይት እና ጋዝ በመሸጥ አገሪቷ ብዙ ገቢ አላት። ጀርመን አንዷ ሸማች ናት።
« ጀርመን የናይሄሪያ ሁለተኛ የኢኮኖሚ ተሻራኪ ሐገር ናት። ለኛ ደግሞ የነዳጅ ዘይቱ ጥያቄ አስፈላጊ ነው።» ሲሉ ያብራራሉ ፊሸር። ምንም እንኳን ናይጄሪያ የተፈጥሮ ባለሀብት ብትሆንም አብዛኛው የአገሪቷ ህዝብ በድህነት ይኖራል። ግማሹ ሕዝቧ እንኳ የመብራት አገልግሎት የለውም። የድርጅቶቹና የመብራት መስመሮቹ ደካማ እና ያረጁ ናቸው።
የኃይል አቅርቦትን በተመለከተ ደግሞ ጀርመን ባለሙያዎች አሏት። ገና እኢአ በ2008 አንጌላ መርክል ከሟቹ የቀድሞ ፕሬዚደንት ኡማሩ ያርአዱአ ጋ ስምምነት ተዋውለዋል። የውሉም ዋና አላማ የጀርመን ድርጅቶች የናይጄሪያን የኃይል አቅርቦት እንዲያስፋፉ ነው። በአንፃሩ ናይጄሪያ እኢአ ከ2014 ዓ ም ጀምሮ የነዳጅ ዘይት ወደ ጀርመን ትልካለች።
« በአሁኑ ሰዓት ሁለቱም አገሮች በርትተዋል ብዬ እገምታለሁ። በተለይ ደግሞ ናይጄሪያ! ይሄ የጊዜ ገደብ የተጠበቀ እንዲሆን ስትል።» ስምምነቱ በዕርግጥ እስካሁን ሲጓተት ቆይቷል። ይሁንና ጉድላክ ጆናታን ፕሬደንት ከሆኑ በኋላ ነገሮች እየተቀየሩ ነው። ጀርመኖች ናይጄሪያ ፀሀይን እና ውሀን በመጠቀም በታዳሽ የኃይል ምንጭ እንድትገለገል እየሰሩ ይገኛሉ። በፖለቲካ ረገዱም ቢሆን በርሊን እና አቡጃ ያላቸውን ግንኙነት ማጠናከር ይፈልጋሉ። ፍሪድሪሽ ኤበርት እሽቲፍቱንግ ከተሰኘው ተቋም- ቶማስ ሜቲግ ይህቺ አገር የፖለቲካ ግጭት ባሉበት አካባቢዎች ከፍተኛ ተሰሚነት አላት ይላሉ።
« ለምሳሌ በኮት ዲቫር ጉዳይ ላይ አልያም አሁን በማሊ ባለው ቀውስ ላይ እንዲሁም በጊኒ ቢሳው! ናይጄሪያ በቀጥታ እና በግልፅ የወታደራዊ ኃይሉን ትታ ለማረጋጋት እና ዲሞክራሲ ለማስፈን ነው የቆመችው። ይሁንና በሰሜን ምስራቅ ናይጄሪያ ቦኮ ሀራም የተሰኘው እስላማዊ አክራሪ ቡድን ጦርነት እንደሚከፍት አሳውቋል። በደቡቡ የአገሪቷ ክፍል የነዳጅ ዘይት መውጣቱን የሚቃወመው ህዝብ የሚያነሳቸው ጥያቄዎችም ገና መፍትሄ አላገኙም። እነዚህ ነጥቦች ፕሬዚደን ጉድላክ ጆናታን ወደ ጀርመን በሚመጡበት ጊዜ ከሚያነሷቸው ርዕሶች ይመደባሉ።
ልደት አበበ
ነጋሽ መሐመድ