1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የጉዞ ማስጠንቀቂያና የኬንያ ቱሪዝም

ዓርብ፣ ግንቦት 8 2006

ናይሮቢ ኬንያ ዉስጥ ዛሬ በደረሰ ፍንዳታ ቢያንስ አስር ሰዉ ሳይገደል እንዳልቀረ ተገለጸ። በርካቶችም ተጎድተዋል። የኬንያ ብሄራዊ የአደጋ መከላከል ዘመቻ ማዕከል ፍንዳታዉ የደረሰዉ በህዝብ ማመላለሻ መለስተኛ አዉቶቡስና ገበያ ዉስጥ መሆኑን ገልጿል። ለፍንዳታዉ እስካሁን ኃላፊነት የወሰደ አካል የለም።

https://p.dw.com/p/1C1VC
Anschlag in Nairobi
ምስል Reuters

ዛሬ ናይሮቢ ዉስጥ በደረሰዉ ሁለት የቦምብ ፍንዳታ አስር ሰዎች መገደላቸዉ ከ70 በላይም መጎዳታቸዉ ነዉ የተገለጸዉ። የመጀመሪያ ፍንዳታ 14 ሰዎችን በሚጭነዉ የሀገሬዉ ሰዎች ማታቱ በሚለዉ መለስተኛ አዉቶቡስ ታክሲ ላይ ሲሆን፤ ሁለተኛዉ ደግሞ ጊኮምባ በተባለዉ ገበያ ዉስጥ ነዉ የደረሰዉ። የኬንያ ፖሊስ እንደሚለዉ ቦምብ ነዉ የተወረወደዉ። ሃኪም ቤት ከተወሰዱት አብዛኞቹም ክፉኛ መጎዳታቸዉ ነዉ የተሰማዉ። ፖሊስ ከተጠርጣሪዎች አንዱን ይዣለሁ ሁኔታዎችም በቁጥጥር ሥር ናቸዉ ቢልም የሕዝቡን መደናገጥ መግታት አልቻለም። ፍንዳታዉ የደረሰዉ ጥቂት የማይባሉ ምዕራባዉያን ሃገራት ለዜጎቻቸዉ የጉዞ ማስጠንቀቂያ በሰጡ ማግስት ነዉ።

አዲሱን የሽብር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ተከትሎ ብሪታንያ በመቶዎች የሚገመቱ ዜጎቿን ከኬንያዉ ሞምባሳ ወደብ እያስወጣች ነዉ። ብሪታንያ፣ ፈረንሳይ፣ አዉስትራሊያ እና ዩናይትድ ስቴትስ የጉዞ ማስጠንቀቂያ ካወጡ በኋላ ልዩ አዉሮፕላን ለዚሁ ጉዳይ መመደቡም ተገልጿል። የብሪታንያ ቱሪስቶች በነጭ አሸዋ በተከበበዉ የሞምባሳ ባህር ዳርቻ የሚያሳልፉትን የመዝናኛ ጊዜ ለጊዜዉ እንዲገቱ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጠይቋል። ዋና መሥሪያ ቤቱ ሎንዶን የሚገኝና በአዉሮጳ ግዙፍ የጉዞ ወኪል ቶምሶን ኤንድ ፈርስት ቾይስ፤ ወደሞምባሳ የሚጓዙ በረራዎችን እስከመጪዉ ኅዳር ወር ድረስ በሙሉ መሰረዙን ተናግሯል። ሞምባሳ ዉስጥ በተደጋጋሚ ጥቃት መድረሱን በመጥቀስም የእረፍት ጊዜያቸዉን በህንድ ዉቅያኖች ዳርቻ ለማሳለፍ የተጓዙ ደንበኞቹን ወደብሪታንያ እየመለሰ መሆኑንም በፅሁፍ ይፋ ባደረገዉ መግለጫ አስታዉቋል። ሞምባሳ የሚገኘዉ ሰን ኤንድ ሳንድ ሆቴሎች ሥራ አስኪያጅ ዳዉድ ናያሙ ቱሪስቶቹ ወደየሀገራቸዉ እንዲመለሱ የሚተወሰደዉ ርምጃ በየራሳቸዉ መንግስታት እንጂ ከኬንያ ወገን የተሰማ አዲስ ነገር እንደሌለ ነዉ የሚናገሩት፤

Anschlag in Nairobi
ፍንዳታዉ የደረሰበት ሥፍራምስል Reuters

«እስከማዉቀዉ ድረስ ባለፉት ቀናት እንደነበረዉ ያለ አሁን የተሰማ ምንም አዲስ ዛቻ የለም፤ እንደሚመስለኝ ዉሳኔያቸዉ ያንን መሠረት ያደረገ ሳይሆን አይቀርም። በአሁኑ ወቅት የተለወጡ ነገሮች የሉም። መንግስትም እንያንዳንዱ ሰዉ በተለይም ሀገር ጎብኚዎች ተገቢዉን ከለላ ማግኘቱን ለማረጋገጥ በጣም እየሠራ ነዉ። ቱሪስቶቹን የማስወጣቱ ዉሳኔ የራሳቸዉ ዉሳኔ ነዉ፤ ከኬንያም ሆነ ከእኛ የተሰጣቸዉ ምንም ዓይነት የሚያስፈራራ ስጋት የለም።»

የኬንያ መንግስት ብሪታንያን ጨምሮ ሌሎቹ ሃገራት የወሰዱትን ርምጃ ተቃዉሟል። ድርጊቱንም ከወዳጆች የማይጠበቅ ሲል በመተቸትም ቅሬታዉን ገልጿል። ከሚዝናኑበት የእረፍት ቆይታ የተናጠቡት ቱሪስቶችም በእርምጃዉ የተደሰቱ አይመስልም። ከእነዚህ አንዷ እንዲህ ነዉ የሚሉት፤

«በጣም ያሳዝና፤ በጣም ያሳዝናል፤ ፍርሃት አልተሰማንም፤ በእርግጠኝነት ሁሉም ከሚገባዉ በላይ ርምጃ እየወሰደ ይመስለኛል። በሙሉ እዚህ መቆየት ነዉ የሚፈልገዉ።»

Somalia Kenia Schiff gekapert mit 21 USA Bürger Maersk Alabama
የሞምባሳ ወደብምስል AP

መንግስት በሞምባሳ ጥበቃዉን ማጠናከሩን የሚገልፁት የሰን ኤንድ ሳንድ ሥራ አስኪያጅ የተጠናከረዉ የፀጥታ ጥበቃ እዚያ የሚገኙ ቱሪስቶቹንም ሆነ ከተማዋን ከማንኛቸዉም ስጋት ለመከላከለ ያለመ እንጂ ሌላ አሳሳቢ ነገር ማስከተል የለበትም ባይናቸዉ። የሀገር ጎብኚዎቹ ከአካባቢዉ መራቅም የኬንያን ኤኮኖሚ ምን ያህል ሊጎዳ እንደሚችል ሲያስረዱ፤

«በቅድሚያ ኤኮኖሚዉን ይጎዳል፤ ከቱሪዝም ብዙ እንደምናገኝ እሙን ነዉ፤ ይህም የአገራችንን ኤኮኖሚ ከሚያንቀሳቅሱት አንዱ ነዉ። በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ የሠራተኞች ሁኔታ ነዉ፤ በርካቶች ከሥራ የሚቀነሱበት ሁኔታ ነዉ የሚኖረዉ ምክንያቱም ምንም የሚሠራ ነገር አይኖርምና።»

በዚህ ምክንያትም ብዙ ቤተሰብ ይጎዳል፤ ከጉዞ ወኪሎች ጀምሮ በየደረጃዉ የሚገኙ ከቱሪስቶች እንቅስቃሴ ጋ የተገናኙ በአነስተኛ ደረጃ የሚገኙ ነጋዴዎች ገቢም ይዳከማል። ከ600ሺ የሚልቁ ኬንያዉያን በቀጥታ በቱሪዝም ዘርፍ ተቀጣሪ ሠራተኞች ናቸዉ።

ሸዋዬ ለገሠ

ነጋሽ መሐመድ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ