የገዋኒ ወረዳ ግጭትና ነዋሪዎቹ
ዓርብ፣ ግንቦት 23 2005
በአፋር መስተዳድር በገዋኒ ወረዳ፥ ከገዋኒ ከተማ ወጣ ብሎ በሚገኝ ገጠራማ መንደር ፖሊስ በያዝነዉ ሳምንት አጋማሽ ላይ በከፈተዉ ተኩስ ቁጥራቸዉ በዉል ያልተወቀ ሰዎች መቁሰላቸዉንና ከመኖሪያ ቀያቸዉ መፈናቀላቸዉን ነዋሪዎች አስታወቁ።የዓይን ምስክሮች እንዳሉት ፖሊስ በሰዎች ላይ ካደረሰዉ ጉዳት በተጨማሪ ተኩሱ ያስደነበራቸዉ ከብቶች ባዝነዉ ጠፍተዋል። ፖሊስ ከዚሕ ቀደም በወሰደዉ ተመሳሳይ እርምጃ ሰዎች መገደላቸዉም ተጠቅሷል።የወረዳዉ የፖሊስ መኮንን የተባሉ ግለሰብን በሥልክ ለማናገር ሞክረን ነበር።መልሳቸዉ ግራ አጋቢ ነዉ። ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
ከዓይን ምስክሮቹ መሐል ገሚሶቹን በስልክ መስመር ጥራት ችግር ምክንያት ማነጋገር አልቻልንም። ጉዳቱ ደረሰብን የሚሉት ደግሞ አማርኛ አይችሉም።አስተርጓሚም አላገኙም።እሳቸዉ ግን ያዩ-የሰመቱን ነገሩን።
ሰበቡ ምስክሮቹ እንደሚሉት ሕገ-ወጥ የሚባል ጦር መሳሪያ ማስፈታት ነዉ።መሳሪያ እንዲፈቱ የሚገደዱት ወይም ሕገ-ወጥ የሚባሉት ደግሞ አንድም ከተማ ዉስጥ አለያም፥ ኢትዮጵያን ከኤርትራ፥ ወይም ከጅቡቲ በሚያገናኘዉ አስፋልት መንገድ ግራ ቀኝ የሠፈሩ ታጣቂዎች ናቸዉ።ትጥቅ የማስፈታቱ ዓለማ ዘረፋን ለመካለከልም ጭምር መሆኑን ነዋሪዎቹ ያምናሉ።
ችግሩ ግን በልማዱ ፌደራል የሚባለዉ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ መንግሥት የሚቆጣጠረዉ ፖሊስ የሚፈፅመዉ-መስራት ካለበት መቃረኑ ወይም እንዲሰራ የሚገባዉን መስራት ባለበት ሥፍራ ሥፍራ አለመስራቱ እንጂ።
ሥም-አድራሻቸዉ እንዲጠቀስ ያልፈለጉት ወይዘሮ እንደሚሉት ፖሊስ ሰዎችን ሲጎዳ ለገዋኔዎች የሰሞኑ አዲስ አይደለም።ከዚሕ በፊትም ፖሊስ እዚያ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎችን ትጥቅ በማስፈታት ሰበብ ያንገላታል። ይደበድባል።ገድሎም ያዉቃል።
ሴትዮዋ እንደሚሉት ፖሊስ በነዋሪዎቹ ላይ ይፈፅማል የሚባለዉን በደል እንዲያቆም ነዋሪዎቹ ለአካባቢ ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ አቤት ብለዉ ነበር።ግን በወይዘሮዋ አገላለፅ መፍትሔ የለም።ደግሞ ይጠይቃሉ።ማነን-እኛ አይነት-ጥያቄ።
የገዋኔ ወረዳ የፖሊስ ባልደረባ ናቸዉ ወደተባሉት ግለሰብ ሥልክ ደወልን።
ትንሽ አይደለም፥ ከብዙ ደቂቃ ምናልባትም ከአንድ ሠዓት የሥልክ ሙከራ በሕዋላ ሥልካቸዉን አነሱ።
ዘጉትም።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሠ