የጀርመን የት/ ሚንስትር የገጠማቸዉ ፈተና
ሐሙስ፣ ጥር 30 2005
የጀርመንዋ የትምሕርት ሚንስትር አኔተ ሻቫን የተማሩበት ዩኒቨርስቲ የዶክትሬት ማዕረጋቸዉን ከገፈፋቸዉ በሕዋላ ሥልጣን እንዲለቁ የሚደረግባቸዉ ግፊት ተጠናክሯል።የዱሰልደርፉ ዩኒቨርስቲ ለሻቫን ሠጥቷቸዉ የነበረዉን የዶክትሬት ማዕረግ የገፈፈዉ በዲግሪ ማሟያ ፅሑፋቸዉ የሌላ ሰዉ ሐሳብን የራሳቸዉ አስመስለዉ ፅፈዋል በሚል ነዉ።የዩኒቨርቲዉ ዉሳኔ ከተሰማ በሕዋላ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች ሚንስትሯ ሥልጣን መልቀቅ አለባቸዉ እያሉ ነዉ።ሻቫን ግን የዩኒቨስርቲዉን ዉሳኔ በመቃወም ማዕረጋቸዉን ለማስመለስ ክስ እንደሚመሠርቱ አስታዉቀዋል።
የካቶሊክ ሥነ-መለኮት እና የማስተማር ሥነ-ጥበብ ዶክትሬታቸዉ ለአኔተ ሻቫን ባለፉት ሰላሳ-አምስት ዓመታት የብዙ ነገራቸዉ አልፋ-ወ-ኦሜጋ ነዉ።ወይም ነበር።እንደ ሊቅ-አስተምረዉበታል።እንደ ፖለቲከኛ የክርስቲን ዲሞክራሲያዊ ሕብረት (CDU) ፓርቲን የሥልጣን ደረጃዎች ተረማምደዉበታል።የፓርቲዉ ሊቀመንበርንና የሐገሪቱን መራሔተ-መንግሥት ቀልብ ስበዉበታል።
የፓርቲ ጓዶቻቸዉን፥ የአባላት-ተከታዮቹን ደጋፍ ሸምተዉበታል።በሥነ-መለኮት ምርምር፥ በሥነ-ማስተማር ጥናት ከትልቁ የትምሕርት ማዕረግ ባይደርሱ ኖሮ፥ ሚንስትር እንኳ ቢሆኑ የትምሕርትና የምርምር ሚንስትር መሆን ባልቻሉ ነበር።
በሃያ-አምስት ዓምት ዕድሜያቸዉ ሥነ-መለኮትን ከማስተማር ጥበብ ጋር ባቀናጀ የትምሕርት መስክ በዚያ ማዕረግ በመመረቅ የመጀመሪያዋ ሴት ወጣት ነበሩ።በዚሕም ሰበብ ለሻቫን ዶክትሬታቸዉ ከፖለቲካ፥ ከሥልጣን፥ ከሊቅነት ማዕረግ መሠረትነቱን በላይ የጥቅል ስብዕና ክብራቸዉም መሠረት ነዉ።
የዱሰልዶርፉ የሐይንርሽ-ሐይነ ዩኒቨርስቲ ከትናንት በስቲያ ማክሰኞ የዶክትሬት ማዕረጋቸዉን ሲገፋቸዉ ሻቫንን ሁሉንም ነዉ ያሳጣቸዉ።ሴትዮዋም ሁሉንም ባንዴ ለሚያሳጣቸዉ ዉሳኔ እጅ አልሰጡም።በፍርድ ቤት እሟገታለሁ-አሉ እንጂ።
ዩኒቨርስቲዉን ለመሞገት መወሰናቸዉ ለዉጤት መብቃቱ አጠራጣሪ ነዉ።በጀርመን ሕግ እንዲሕ አይነቱን ጉዳይ አጣርቶ ብይን መስጠት ብዙም አልተለመደምና።ይሁንና በፍርድ ቤቱ ዉጣ ዉረድ መሐል ሻቫን አባል የሆኑበት የሜርክል መንግሥት ዘመነ-ሥልጣን አብቅቶ ከስምንት ወር በሕዋላ ምርጫ ይደረግ ይሆናል።
የመመረቂያ ፅሑፏን (ዲዘርቴሽን) የመረመረዉ አስራ-አምስት ፕሮፌሰሮች ያሉበት ኮሚቴ ግን ሚንስትር ሻቫን በፁሁፋቸዉ ዉስጥ የሌላ ሰዉ ፅሑፍ ወይም ሐሳብ ሳይጠቅሱ የራሳቸዉ አስመስለዉ ማቅረባቸዉን አረጋግጧል።ሻቫን የዶክትሬት ማዕረጋቸዉ ይገፈፍ የሚለዉን ሐሳብ ከአስራ-አምስቱ ፕሮፌሰሮች አስራ ሁለቱ ሲደግፉት፥ አንዱ ድምፃቸዉን አቅበዋል።ሁለቱ ተቃዉመዉታል።
ሻቫን አጭበርብረዋል፥ እና ማዕረጋቸዉ ይገፈፍ የሚለዉ ሐሳብ በአስራ-ሁለት ለ-ሁለት ድምፅ ፀደቀ።ከዚሕ በሕዋላ ነበር ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሚንስትሯ ላይ ቁጣቸዉን ያዥጎደጎዲት።የዋናዉ ተቃዋሚ የሾሻል ዲሞክራቶቹ (SPD) ፓርቲ ዋና ፀሐፊ አንድሪያ ናሕሌስ ቀዳሚዋ ናቸዉ።«የዶክትሬት ማዕረጋቸዉ እዉቅና ከተነፈገዉ በሕዋላ፥ እሳቸዉ ጥሩ ምሳሌም፥ ተዓማኒም አይሆኑም።ሥለዚሕ ሥልጣን መልቀቅ አለባቸዉ።»
የአረንጓዴዎቹ ፓርቲ የምክር ቤት እንደራሴዎች ተጠሪ ዩርገን ትሪቲን ቀጠሉ፥«እሳቸዉ ከእንግዲሕ እዉነተኛዉን የጀርመንን የሳይንስና ምርምር ገፅታን ለመወከል ታማኝነቱ የላቸዉም።»የግራዎቹ ፖለቲከኞችም አሰለሱ።
መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ፅፈት ቤት ግን በቃል አቀባያቸዉ በኩል መንግሥት የዩኒቨርስቲዉን ዉሳኔ ያከብራል ከማለት ሌላ የመራሒተ መንግሥቷን ዉሳኔ አላሳወቀም።የሜርክል መንግሥት እንዲሕ አይነት ቅሌት ሲገጥመዉ ያሁኑ ሁለተኛዉ ነዉ።ከሁለት ዓመት በፊት የያኔዉ መከላከያ ሚንስትር ካርል ቴዎዶር ሱ-ጉተን በርግ በተመሳሳይ ቅሌት ሥልጣናቸዉን ለመልቀቅ ተገደዉ ነበር።ሻቫን ያኔ የሱ-ጉተንበርግን ምግባር «አሳፋሪ» ብለዉት ነበር።ዛሬስ?
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ