የጀርመንዋ የግብርና ሚንስትር በኢትዮጵያ
ረቡዕ፣ ሚያዝያ 30 2005ሚንስትሯ ከጁሐንስበርግ ወደ አዲስ አበባ ከማቅናታቸዉ በፊት ለዶቸ ቬለ በሥልክ በሰጡት ቃለ መጠየቅ እንዳሉት ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ጋር ከሚነጋገሩባቸዉ ርዕሶች የምግብ ዋስትናን ማስጠበቅና የመሬት ባለቤትነት ቀዳሚዎቹ ናቸዉ።
የጀርመንዋ ግብርና ሚኒስትር ኢልዘ አይግነር፤ በአፍሪቃ ሰብልን ለነዳጅ ከማዋል ይልቅ ለምግብ የሚሆን እንዲዉል ማድረግ ቅድምያ ሊሰጠዉ የሚገባ ጉዳይ ነዉ የሚል ሃሳብ አላቸዉ።ምክንያቱ ከምድር ወገብ በስተደቡብ በሚገኙ አገራት አበረታች የኢኮኖሚ እድገት ቢታይም፤ አሁንም 870 ሚሊዮን ህዝብ በምግብ እጥረት ይቸገራልና ይላሉ ሚንስትሯ።
«በዚህም ምክንያት በአፍሪቃ አገራት ሰብልን ለምግብነት ማዋል ቅድሚያ ሊሰጠዉ የሚገባ ጉዳይ ነዉ። (ለነዳጅ ምትክ) ይዉላል መባሉ ተቀባይነት አይኖረዉም።
ሚኒስትሯ ትናንት በደቡብ አፍሪቃ ፕሪቶርያ ጉብኝታቸዉ፤ በአፍሪቃ የነዳጅ ምርትን ከሚሰጥ የሰብል ምርት ይልቅ የምግብ ምርትን ማስቀደሙ ወሳኝ መሆኑን በመግልጽ በቆሎን ለነዳጅ ምርት ከምናበቅል ይልቅ፤ ሌሎች የምግብ አዝርቶችን ማምረት ወሳኝነቱን አስረድተዋል። በአፍሪቃ የዘመናዊ ግብርና መገልገያ ዘዴዎችን እና የግብርና ዘዴ አዋቂዎች እጥረትን በሚመለከት ከዶቼ ቬለ ለቀረበላቸዉ ጥያቄ ሚኒስትሯ ጥምሩን የጀርመኑን ዘዴ በምሳሌነት ጠቅሰዋል።
«በነዚሕ ሐገራት ምርታማነትን ለማሳደግ ቲወሪን ከተግባራዊ ሙከራ ጋር ያጣመረ የትምሕርትና የሥልጠና ሥርዓት መዘርጋት ጠቃሚ ነዉ። በተግባር ላይ ያተኮሩ ግባአቶችን ማዳበር እና ብዙዉን አምራች ለማዳረስ አሠልጣኞችን ማሠልጠንም ጠቃሚ ነዉ።»
በአፍሪቃ በግብርናዉ ዘርፍ አስፈላጊዉ ነገር ጥሩ ዘር፤ ማዳበርያ፤ የተስተካከለ የመሰረተ ልማት፤ አዉታር፥ መስኖ የግብርና መሳርያ እና ሥልጠና ወይም እዉቀት መሆኑን ሚንስትሯ ገልጸዋል። አፍሪቃ ለማደግ እጅግ ከፍተኛ አቅምና፤ በእድገትዋም አስደሳች እና የሚያበረታታ እርምጃን ብታሳይም፤ በቀጣይ ከፍተኛ የህዝብ ቁጥር መጨመር እና አየር ንብረት በከፍተኛ ሁኔታ መለወጥን የመሳሰሉ ከባድ ፈተናዎች ትጋፈጣለች። ኢልዘ አይግነር ምርታማነትን ለማሻሻል ይላሉ፤
«ለየትኛዉም የአፍሪቃ ሐገር ቢሆን መሠረታዊዉ ጉዳይ የተረጋጋ ፖለቲካዊ ግንኙነትና ግልፅ የሆነ የመሬት ባለቤትነት መብት መኖር ነዉ።ከዚሁ ጋር የአመራረት ሥልትን ማዳበር፥ እዉቀትን ማስረፅና ማሳደግም አስፈላጊዎች ናቸዉ።በዚሕ ምክንያት እኔ እንደማምነዉ ከየአካባቢዉ የአምራቾች ማሕበራት መዋቅር ጋር ግንኘነት መመሥረት ጠቃሚ ነዉ።ምክንያቱም ማሕበራቱ አነስተኛ አምራቾችን የሚያስባስቡና በርካታ ሠብል የሚያመርቱም በመሆናቸዉ ነዉ።የመሬቱ ምርታማነት የሚጠበቀዉና ለብዙ ጊዜ አገልግሎት የሚሠጠዉ ደግሞ የገበሬዉ የመሬት ባለቤትነቱ ሲረጋገጥለት ነዉ።»
በአፍሪካ ለእርሻ ምርት አመቺ የአየር ጸባይ፤ ለም መሪት ቢኖሮም፤ በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዳልዋለ ሚኒስትር አይግነር ፤ በደቡብ አፍሪቃ ጉብኝታቸዉ ሳይጠቅሱ አላለፉም። እጅግ ደሃ ከሚባሉ ሀገሮች የምትመደበዉ ኢትዮጵያ፤ የሰብል ምርትን የማቅረብ ከፍተኛ አቅም ቢኖራትም እስካሁን ህዝብዋን ሙሉ በሙሉ መመገብ አልቻለችም።ኢልዘ አይግነር አንድ ሀገር ይላሉ፤
«አንድ ሀገር 40% የሚሆነዉ ህዝቧ በምግብ እጥረት የሚሰቃይ ከሆነ የምግብ አቅርቦትን አስተማማኝ ደረጃ ማደረስ ዋንኛ እና ቅድምያ ሊሰጠዉ የሚገባ ጉዳይ ነዉ።»
ኢትዮጵያ ዉስጥ መሬትን በሊዝ ለማኮናተር ሲባል ነዋሪዎች ከመኖርያ ቀያቸዉ ተፈናቅለዋል የሚባለዉን ጉዳይ ምን አስተያየት አልዎት? ተብለዉ ለቀረበላቸዉ ጥያቄ የጀርመንዋ ግብርና ሚኒስትር ኢልዘ አይግነር
«ይህን ጉዳይ በሚመለከት መነጋገር እፈልጋለሁ። ኢትዮጵያም የተባበሩት መንግስታትን ህግ እንዳልጣሰች ተስፋ አደርጋለሁ።ለግብርና የሚሆን መሬት ላይ መዋለ ንዋይ ማፍሰሱ የተወላጆችን «የነዋሪዎችን» መሬት እንዲነጠቁ እና እንዲፈናቀሉ ዳርጎ ከሆነ፤ ትክክል አይደለም።ያ።በተለይ ደግሞ(ለባለሐብቶች የሚሰጠዉ) ለም መሬት ከሆነ የአገሪቱንም ጥቅም አያስጠብቅም»
የጀርመንዋ የግብርና ሚኒስትር በኢትዮጵያ ጉብኝታቸዉ በጀርመን የሚደገፍ የእርሻ፤ የጥናትና፤ የሙከራ ማዕከልን ይጎበኛሉ።
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሃመድ