የዶይቸ ቬለ የአማርኛው አገልግሎት የወርቅ ኢዮቤልዩ
ማክሰኞ፣ መጋቢት 8 2007ዩናይትድ ስቴትስ በቪየትናም መጠነ ሰፊ ጦርነት ያፋፋመችበት ፤ ሶቭየቶች በበኩላቸው ፣ በአዳጊ አገሮች ተጽዕኖአቸውን በማጠናከር ፣ የራሳቸውን ርእዮት ለማስፋፋት የተንቀሳቀሱበት ዘመን ነበረ። በዩናይትድ ስቴትስ በተለይ የጥቁር አሜሪካውያን የእኩልነት ጥያቄና ትግል በአደባባይ መታየት የጀመረው በዚያ ዘመን ነው ። ለምሳሌ፣ ባለፈው ሳምንት 50 ዓመት የደፈነውን፤ በእነ ዶክተር ማርቲን ሉተር ኪንግ መሪነት በሴልማ ፤ አላባማ የተደረገውን የሲቭል መብት ታጋዮች ሰልፍና ያጋጠመውን የኃይል ርምጃ ያስታውሷል።
በምዕራብ አውሮፓና በሰሜን አሜሪካ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም፣ በተለይ ወጣቱ ትውልድ፣ አንዳንድ የመንግሥት ፖሊሲዎችን በመቃወም፤ ድምፅ ማሰማትና ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ የጀመረበት፤ «ፖፕ» የተሰኘው ተወዳጅ ዘመናዊ ሙዚቃ በዜማና ግጥም የተወደደበትን አሻራ ያሣረፈውም ፣ በዚሁ በ 1960 ዎቹ ዓመታት ነው። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የተቃውሞ ዘፈኞች (ፕሮቴስት ሶንግስ ) የሚሰኙት መቅረብ የጀመሩት፣ ወጣቱ በአለባበስ ፤ በአኗኗርና በመሳሰለውም ፣ በተደላደለው የከበርቴው ሥርዓት ላይ አመጽ ቢጤ ያሳየበትም ያ ወቅት ነበር።
የዩናይትድ ስቴትስ ተጓዳኝ የጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ (ምዕራብ ጀርመን)፣ የኤኮኖሚ ተዓምራዊ ዕድገት (Wirtschaftswunder) የተሰኘውን ያስመዘገበችበት ፤ ህዝቧም ከሁለተኛ የዓለም ጦርነት ፍጻሜ በኋላ የተድላ ኑሮ መኖር የጀመረበት ጊዜ ነው ፣ 1965 ጎርጎሪዮሳዊው ዓመት! ያኔም ነው ታዲያ ምዕራብ ጀርመን፤ ከዓለም ማሕበረሰብ ጋር ጥሩ ግንኙነት ለመመሥረት የተነሣሣችውና በተለያዩ ቋንቋዎች በዓለም ዙሪያ በአጭር ሞገድ የራዲዮ ፕሮግራሞችን ማሠራጨት የጀመረችው። ከጀርመን ፌደራል ሪፓብሊክ በአማርኛ ለማሠራጨት ያነሣሣ ምክንያት ምን ነበር?
ተክሌ የኋላ/አርያም ተክሌ
አዜብ ታደሰ