1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዳርፉር ስደተኞችና ቻድ

ቅዳሜ፣ ሚያዝያ 14 1998

ብዙ ማነጋገር የያዘው የቻድ ውዝግብና የዳርፉር ስደተኞች ዕጣ ፈንታ

https://p.dw.com/p/E0im
በቻድ የሚገኙ የዳርፉር ስደተኞች
በቻድ የሚገኙ የዳርፉር ስደተኞችምስል picture-alliance/dpa

የቻድ መንግሥት ለለውጥ የተባበረው ያማፅያን ቡደን ቡድን በመዲናይቱ ንጃሜና የሰነዘረውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ደመሰሰ። ይሁንና፡ ፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ ከሥልጣን እስኪወርዱ ድረስ የቻድ ጊዚያዊ ሁኔታ የሚረጋጋ እንደማይመስል የፖለቲካ ታዛቢዎች ገምተዋል። ምክንያቱም፡ ፕሬዚደንቱና ዓማፅያኑ ከሁለት ሣምንታት በኋላ በሀገሪቱ የሚደረገውን ፕሬዚደንታዊ ምርጫ እንደ ወሳኝ ርምጃ በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉና። ኢድሪስ ዴቢ ለፕሬዚደንታዊው ምርጫ በዕጩነት ለመቅረብ ዕቅድ አላቸው። ይህንኑ ዕቅዳቸውን ካስታወቁ ወዲህ በሀገር ውስጥ ብርቱ ተቃውሞ ገጥሞአቸዋል። የፕሬዚደንቱን ለሦስተኛ ጊዜ በዕጩነት የመቅረቡን ዕቅዳቸው የማከላከሉ ጥያቄ ነው ለነገሩ የጎሣና የፖለቲካ ዓላማቸው እጅግ የተለያዩትን ያማፅያን ቡድኖችን በአሁኑ ጊዜ አንድ ኅብረት እንዲፈጥሩ ያደረጋቸው። እአአ በ 1990 ዓም የቀድሞውን የቻድ ፕሬዚደንት ሂስኔ ሀብሬን በመፈንቅለ መንግሥት ከሥልጣን ያወረዱት ዴቢ ሁለት ጊዜ በዴሞክራሲያዊ ዘዴ ቢመረጡም፡ የሀገሪቱ ሕገ መንግሥት ለሦስተኛ ጊዜ በዕጩነት እንዲወዳደሩ አይፈቅድላቸውም። ዴቢ ለሦስተኛ ጊዜ ሀገሪቱን የሚያስተዳድሩበት ድርጊት ሕገ ወጥ ብቻ ሳይሆን ቻድን ምሥቅልቅሉ ሁኔታ ላይ እንደሚጥላት ነው የተቃዋሚ ቡድኖች የሚያስጠነቅቁት። ካለፉት ጥቂት ወራት ወዲህ በዓማፅያኑ ቡድን ከተጠቃለሉት ለውጥ ፈላጊዎቹ ቻድያውያን መካከል ቀደም ባሉት ጊዚያት ፕሬዚደንት ዴቢን ይደግፉ የነበሩትና ልክ እንደ ፕሬዚደንቱ የዛግዋ ጎሣ አባላት የሆኑት አንዳንዶቹ ዴቢ በዳርፉር ሱዳን ለሚኖሩትና ከዐረባውያኑ ሚሊሺያዎች ጥቃት የተሰነዘረባቸው የዛግዋ ጎሣ አባላት በቂ ድጋፍ አልሰጡም በሚል ይወቅሱዋቸዋል። ፕሬዚደንት ዴቢ ደጋፊዎቻቸው እየከዱዋቸው ለለውጥ ወደተባበረው ያማፅያን ቡድን ቢገቡም፡ በዕጩነት ለመቅረብ በወጠኑት ዕቅዳቸው እንደፀኑ ለመቆየት ነው የወሰኑት። ያማፅያኑ ጉድኝት በኃይሉ ርምጃ ለውጥ ለማስገኘትና በሀገሪቱም ነፃና ግልጹን ምርጫ ለማስደረግ መቻሉ ግን አጠያያቂ እንደሆነ ነው የሚገኘው። ለምን ቢባል፡ ዴቢ አሁንም፡ በኃይሉ ተግባር የሥልጣን ለውጥ የሚደረግበት ሁኔታ የቻድን ብቻ ሳይሆን ያካባቢውንም ፀጥታ ያናጋል የምትለው የፈረንሣይ ድጋፍ አልተለያቸውምና። እንደሚታወቀው፡ ፈረንሣይ ካለፉት በርካታ ወራት ወዲህ ቻድ ውስጥ አንድ ሺህ ሁለት መቶ ወታደሮች ያሠማራች ሲሆን፡ ከነዚሁ መካከል አንድ ሺህ የሚገኙት ንጃሜና ውስጥ ነው። ዴቢ የፈረንሣይን ድጋፍ ባይገኙ ኖሮ የሰሞኑን መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ማክሸፍም ሆነ መደምሰስ ባልተሳካላቸው ነበር፤ ምንም እንኳን፡ ፓሪስ ለቻድ ይህንኑ ድጋፍ መስጠትዋን ብታስተባብልም።
ቻድ በሀገርዋ ለታየው ውዝግብ የሱዳን እጅ እንዳለበት ትወቅሳለች። የጎረቤት ሱዳን መንግሥት በቻድ የሚንቀሳቀሱትንና በብዛትም ሙሥሊም የሆኑትን ዓማፅያንን ይረዳል በሚል ቻድ ክስ በማሰማትዋ ውዝግቡ ከቻድ አልፎ መላውን አካባባኢውን እንዳያጣቅስ የፖለቲካ ታዛቢዎች ሠግተዋል። የሱዳን መንግሥት ለለውጥ ለተባበረው ያማፅያን ግንባር የጦር መሣሪያ እና ሌላም ቁሳቁስ በርዳታ እንደሰጠ ዴቢ በማስታወቅ፡ ከዚች ሀገር ጋር ዲፕሎማቲያዊ ግንኙነት በይፋ አቋርጣለች። ሱዳን ይህንን የቻድ ወቀሳ መሠረተ ቢስ ስትል አስተባብላዋለች። ይህንን የቻድ ርምጃ የዩኤስ አሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚንስቴር ቃል አቀባይ ሶን ማኮርማክ ትክክለኛ አለመሆኑን ገልፀዋል። « የቻድ መንግሥት ከሱዳን ጋር የሚያዋስነውን ድንበር መዝጋቱንና ከሱዳን መንግሥትም ጋር ዲፕሎማቲያዊ ግንኙነቱን ማቋረጡን ሰምቼአለሁ። ይሁንና፡ ከትቂቱ ተጨማሪው የመገናኛ ዘዴ ቢኖር የተሻለ ነው ብለን እናስባለን። ከጥቂቱም ተጨማሪ ውይይት ቢኖር እንመርጣለን። »
ይኸው ቻድ የወሰደችው ርምጃ በተለይ በምሥራቃዊው ቻድ በሚገኙት ወደ ሁለት መቶ ሀምሳ ሺህ በሚጠጉት የዳርፉር ስደተኞች ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳያሳርፍ አሥግቶዋል። ምክንያቱም ፕሬዚደንት ኢድሪስ ዴቢ በቻድ ለሚገኙት ለሱዳን ስደተኞች ዓለም አቀፉ ኅብረተ ሰብ እስከ ሰኔ ወር መጨረሻ ድረስ ሌላ መጠለያ ቦታ እንዲያዘጋጁላቸው ጊዜ ሰጥተዋል። በዚህም ላይ ማኮርማክ የሰጡት አስተያየት፡
« የቻድ መንግሥት በአውሮጳ ኅብረትና ዓለም አቀፉ ኅብረተ ሰብ በነደፈው ውል እንደተጠቀሰው ለዳርፉር ስደተኞች ከለላ የሚሰጥበትንና ርዳታ የሚያገኙበትንም መንገድ ክፍት የሚያደርግበት ኃላፊነቱን እንዲወጣ እናሳስባለን። ስደተኞቹ ተገቢውን እንክብካቤ ማግኘታቸው መረጋገት ይኖርበታል። »