የ«ደዘርቴክ » የወደፊት ዕጣ
ሐሙስ፣ ሰኔ 28 2004የሚተከሉ በፀሐይና ነፋስ ኃይል የሚሠሩ የኤሌክትሪክ ማመንጫ አውታሮች ላካባቢው ህዝብ ብቻ ሳይሆን፣ ለአውሮፓም ጠቀሜታ እንዲሰጡ ነው የሚፈለገው። የ«ደዘርቴክ« ጽንሰ ሐሳብ ፣ የመካከለኛው ምሥራቅና የሰሜን አፍሪቃ አገሮች የተረጋጋ ፖለቲካ ለአቅዱ መሥመር ወሳኝነት አለው። የደዘርቴክ የወደፊት ዕጣ-ፈንታ፣ በሚል ርእስ፣ የዶቸ ቨለ ባልደረባ፣ ኢንዛ ቭሬደ ያቀረበችውን ዘገባ ፤ ተክሌ የኋላ እንደሚከተለው ያቀርበዋል።
ባለፈው ዓመት ፤ ከአውሮፓ ማዶ ሜድታራንያን ጠረፍ የሚገኙ በተለይ የሰሜን አፍሪቃ አገሮች፤ መረጋጋት አልታየባቸውም ነበር። ውዝግቦች፤ ከመባባስ በስተቀር፤ ጋብ ያሉበት ሁኔታ ገና አልታየም። ታዲያ በተጠቀሰው አካባቢ፣ የታዳሽ ኃይል ምንጭ አውታሮች መትከሉ፣ ያዋጣል ወይ?የሚል ጥያቄ ከአውሮፓ በኩል መቅረቡ አልቀረም።
ደዘርቴክ የተባለው የኩባንያዎች ጥምረት፣ ከሞሮኮ የፀሐይ ኃይል ነክ ተቋም ጋር ባደረገው ስምምነት፣ ከ 2014 አንስቶ፣ የታዳሽ ኃይል ምንጭ በማስተላለፊያ ዘዴ ወደ እስፓኝ ለማሻገር አቅዶ ነበር።
ከ«ላይብኒትዝ » ተቋም፤ የዓለም አቀፍና አካባቢያዊ ጥናት ባለሙያ Sören Scholvin ፕሮጀክቱ አጠራጣሪ ነው ይላሉ።
1,«የአልጀሪያው በተለይ በፖለቲካ ውዝግብ ሳቢያአስቸጋሪነቱ ግልፅ ነው። ሞሮኮና አልጀሪያ ያላቸው ግንኙነትም ያማረ-የሠመረ እንዳልሆነ የታወቀ ነው።
የፀሐይ ኃይል ምንጭን፤ ከአልጀሪያ ወደ አውሮፓ ለመሻገር፤ መሥመሩ በሞሮኮ በኩል የሚያልፍ በመሆኑ፣ የ MENA ፕሮጀክት፣ እንዲሣካ፣ ፖለቲካውን የሚያረጋጋ ሁኔታ ሊኖር ይገባል።»
አውሮፓ ፣ መካከለኛው ምሥራቅና ሰሜን አፍሪቃ ያላቸውን መልክዓ-ምድራዊ አቀማመጥ ሲያስቡት፣ ለፕሮጀክቱ መሣካት የአካባቢው አገሮች ሁሉ ማለፊያ ትብብር እንዲያደርጉ ግድ ይላል። አምና የተቀጣጠለውና የተዛመተው የለውጥ እንቅሥቃሤ በ «ደዘርቴክ» ኩባንያዎች ጥምረት ዘንድ ያልታሰበ ሁኔታ ነበር። ያም ሆነ ይህ ለጊዜው፣ በጥቅሉ ሳይሆን ፤ ካንዳንድ ሞሮኮን ከመሳሰሉ አገሮች ጋር በተናጠል፣ ትብብሩ የቀጠለ ሲሆን፤ ሊቢያንና ግብፅን በንድፉ ያካተተው አቅድ ባለመረጋጋት ሳቢያ ለጊዜው አልተተኮረበትም። በረጅሙ እቅድ ግን የማይቀር ነው።
ተክሌ የኋላ፣
ሒሩት መለሰ