1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የደቡብ አፍሪቃው «ዑቡንቱ» ፣

ረቡዕ፣ የካቲት 9 2003

በሥነ ቴክኒክ የመገናኛ አውታሮች መስፋፋት ረገድ፣ ከሁሉም ክፍላተ ዓለም በአዝጋሚነት የሚጠቀሰው የአፍሪቃው ክፍለ ዓለም ነው።

https://p.dw.com/p/R1dU
የ«ዑቡንቱ» ማኅበረሰብ ድረ ገጽ በፎቶግራፍ፣ምስል www.ubuntu.com

በትምህርት ፤ በጤና አጠባበቅ ፣ በንግድና ኤኮኖሚ ፈጣን እንቅሥቃሴ ለማድረግ ፣ የተንቃሳቃሽ ስልክና የኢንተርኔት ጥምረት መስፋፋት ፣ ለአፍሪቃውያን ፣ እጅግ ተፈላጊ መሆኑ ቢነገርም፣ በተለይ አምባገነን መንግሥታት ፣ ህዝብን አደንቁረው መግዛት ስለሚሹ፣ ይህ የሥነ ቴክኒክ ውጤት እንዲስፋፋ ሳይሆን፣ እንዲገታ ነው የሚፈልጉት። ይህን የሥነ-ቴክኒክ ጸጋ ፣ እርግጥ ነው ለዘለቄታው የውጭ ጥገኛ ሳይኮን ፤ አገልግሎቱ እንዲስፋፋ ማድረግ የሚበጅ መሆኑ የሚያጠራጥር አይደለም። ደቡብ አፍሪቃ፣ ከተጠቀሰው አከራካሪ ችግር ሌላ ሞባይል እንዲስፋፋ በማደረግ ረገድ ከሌሎቹ የአፍሪቃ አገሮች በላቀ ደረጃ ላይ ነው የምትገኘው። ጤናይስጥልኝ እንደምን ሰነበታችሁ? በዛሬው ሳይንስና ኅብረተሰብ ቅንብራችን፤ በደቡብ አፍሪቃ በሞባይልና ኢንተርኔት አገልግሎት ጥምረት ረገድ ፣ የሚደረገውን እንቅሥቃሤ ይሆናል የምንዳስሰው።

ከሰሜኑ ንፈቅ ክበብ በኩል ሲታይ፣ የአፍሪቃው ክፍለ ዓለም የኢንተርኔት ድርቅ የመታው ምድረበዳ ነው ማለት ይቻላል። የኢንተርኔት መስመር ማግኘት የሚያስችል የስልክ መስመር ያለው ከስንት አንዱ ነው። በመሆኑም የሞባይሉ ሥርጭት እጅግ መስፋፋቱን ቀጥሏል። በዚህ የመገናኛ ዘዴ ደግሞ ፣ ገንዘብ ከቦታ- ቦታ ለማዘዋወር፣ የጤና ይዞታን የሚመለከት ዘገባ ለማቅረብ ፣ ሂሳብን የመሰለ ትምህርት ለመቅሰምም ቢሆን ጠቀሜታ አለው። አፍሪቃ ውስጥ እንዲህ ዓይነቱን ተግባር በሞባይል ማከናወን እየተለመደ መጥቷል። ለእንዲህ ዓይነቱ የተሣካ አሠራር ቁልፉ ገንዘብ ለሌላቸው ያመቻቸው የኢንተርኔት የነጻ አገልግሎት ክፍል ነው። ታላላቆቹ የኢንተርኔት የተለያዩ ፕሮግራሞች (ሶፍትዌር )ባለቤቶች በነጻ የሚያድሏቸውን ፕሮግራሞች በሰፊው ለመሣራጨት ውድድር የያዙ ይመስላል ። አፍሪቃውያን የመብት ተቆርቋሪዎች ይህ አዲስ ዓይነት ቅኝ አገዛዝ ነው በማለት እርምጃውን ያወግዛሉ። ያም ሆኖ፣ «ዑቡንቱ» የሚል ስያሜ የተሰጠው የሞባይል ዓይነት በሰፊው በመሠራጨት ላይ ነው።

«ዑቡንቱ»፤ በዙሉና እንጦሳ (Xhosa) «ሰብአዊነት» እንደማለት ነው። እኔነቴን በሌሎች በኩል ነው ያገኘሁት የሚል ትርጓሜም ይኖረዋል። ታዲያ ይህ አባባል የአንግሊካውያኑን መንፈሳዊ አባት አባ ዴዝመድ ቱቱን ማስቆጣቱ አልቀረም ።

««ዑቡንቱ» «ዑቡንቱ» «ዑቡንቱ? » ዝም በሉ ይህን ቃል እንደገና በፍጹም እንዳትጠቀሙበት!» ዴዝመንድ ቱቱ ቃሉን ይመስላል ያልወደዱት። የዘለፉት፣ አንዳንድ የማይመራመሩና የኅይል ተግባር የሚፈጽሙ ያሏቸውን የሀገራቸውን ሰዎች ነው። በተረፈ የሥነ ቴክኒክን መስፋፋትና ጠቀሜታውንም ይደግፋሉ። በአፍሪቃ የተሠራው ዑቡንቱ ሶፍትዌር ከአፍሪቃም ውጭ ሰፊ ገበያ ቢያገኝ ቱቱ የሚኮሩበት እንጂ የሚያፍሩበት ላይሆን ይችላል።

ዑቡንቱ፣ አንድ የፈጠራ ውጤት ነው። አፍሪቃ ውስጥ በሞባይል ገንዘብን መላክ የሚቻልበትን ሁኔታ አሳክቷል። የስልክና ኢንተርኔት አጠቃቀም ዘዴ እንዲቃለል አድርጓል። በኬንያ የተዘጋጀ የጤና አጠባበቅን የሚመለከት ሶፍትዌር ፣ መደበኛ የህክምና ዘገባ ከዑቡንቱ ጋር ተጣምሯል። ማብራሪያውም ፣ MRS በሚል የአንግሊዝኛ ምህጻር በሚታወቀው፣ በቁሳቁስ ነኩ የምርምር ማኅበረሰብ በኩል የተዘጋጀ ነው። በደቡብ አፍሪቃ የመንግሥት የሆነው፣ የሳይንስና ሥነ-ቴክኒክ፣ እንዲሁም የኢንዱስትሪ ምርምር ማዕከል(CSIR) ለተማሪዎች ቀላል በሞባይል የሚሠራ የሂሳብ የቤት ሥራ ረድፍ አዘጋጅቷል። ይህም ማለት ማንኛውም ሰው፣ በ SMS ፣ በ 4 ማዕዘን ቅርጽና የኮከብ ምልክት ፣ የቤት ሥራን መቆጣጠር ይቻላል። በተጠቀሰው ማዕከል ነጻ የመረጃ ሶፍትዌር እንዲዘጋጅ ያበቁት ሴሎ ሌሆንግ ፣ በዚህ ሥራቸው የሚኩራሩ ሲሆን ፣ በኢንተርኔት በተዘረጋው የሳይንስ መድረክም (WWW ዳት ቺሲምባ ዳት ኮም) በተሰኘው ማለት ነው፣ እንዲገናኙ ተደርጓል። ሴሎ ሌሆንግ ስለ ዑቡንቱ እንዲህ ይላሉ።

2, «በዑቡንቱ ደስ የሚለው ነገር፤ ለተጠቃሚዎች አመቺ መሆኑ ነው። ላዩ ለ Linux መርኀ-ግብር አጠቃቀም እንዲያመች ሆኖም ነው የተሠራው። «ላይነክስ» ለተራው ሰው ውስብስብ ያለና አስቸጋሪ ነው። ይሁን እንጂ፣ ዑቡንቱ በስዕላዊ አገላለጽ፣ መመሪያውን በማቅለል፤ በትክክለኛው ጊዜ፣ ልዩ ትምህርት ሳያስፈልገው የላይነክስን አጠቃቀም ተግባራዊ ለማድረግ አስችሏል።»

የኢንተርኔት ነጻ ትምህርታዊ የመረጃ ክፍል ሊቅ ሴሎ ሌሆንግ ነበሩ ይህን ያሉት።

የዑቡንቱ ፈልሳፊ፣ የደቡብ አፍሪቃ የኢንተርኔት አስተዋዋቂ የሚሰኙት ማርክ ሻትልወርትስ ናቸው። ለምሥጢር ጥበቃ አስተማማኝ ሶፍትዌር በማቅረብ ፣ ገና 30 ዓመት ሳይሞላቸው እልፍ አእላፍ ሚሊዮን ብር በመዛቅ የጠነጠኑ ሀብታም ሻትልወርስ ፣ ከአፍሪቃ የመጀመሪያው የኅዋ ቱሪስት ለመባልም የበቁ መሆናቸው አይዘነጋም። እኒህ የጠነጠኑ ሀብታም በከፊል ገንዘባቸው ፣ የኢንተርኔት ነጻ ትምህርታዊ መረጃዎች እንዲዘጋጁ ያበቁ መሆናቸውም ይነገርላቸዋል። አፍሪቃ፤ ከሌሎች ክፍላተ-ዓለም ጋር ሲነጻጸር በኢንተርኔት አገልግሎት ረገድ የመጨረሻ መሆኑ ያላስደሰታቸው ሻትልወርትስ፣ «ፍሪደም ቶስተር» የተባለ፣ አንድ የበጎ አድራጎ ድርጅት በማቋቋም፤ ገንዘብ በመክፈል ከግዙፍ ሣጥን ጠርሙስ መጠጥ መውሰድ በሚቻልበት ሁኔታ፣ በታላላቅ ሱቆች መግቢያ ላይ ከተዘጋጀ ሣጥን ሰዎች በነጻ ሶፍትዌር ሲዲ እየወሰዱና እያባዙም ማሠራጨት እንዲችሉ አብቅተዋል። በሞባይል አማካኝነት ይህን ነጻ ትምህርታዊ የመረጃ ሶፍትዌር ያሰናዱት እስቲቭ ሶንግ የተባሉት ናቸው።

3, « የምንኖርበት ዘመን፣ ዕድገት የሚገኘው በዕውቀትና ሐሳብን በማመንጨት ብቻ ነው። ጥሩ የመገናኛ መረብ መዘርጋትም ወሳኝነት አለው። ሐሳብ የተከማቸብትን የዕውቀት ጎተራ መጎብኘት ማግኘትና ማፍለቅም መቻል አለበት። ይህ፣ ለኤኮኖሚና ማኅበራዊ ዕድገት መሻሻል ወሳኝነት ያለው ነው።»

እስቲቭ ሶንግ እንደሚሉት፤ አፍሪቃ በልማት ወደኋላ የቀረው፣ የሥነ ቴክኒክ አውታሮች ስላልተዘረጉለት ነው። ከቤቱ በቀጥቴታ በኢንተርኔት መገልገል የሚችለው ስንቱ አፍሪቃዊ ነው? የሆነው ሆኖ ግን በቀጥታ እስከቤት ድረስ የሚዘረጋው የስልክ መሥመር የግድ አስፈላጊ ካልሆነበት ዘመን የተደረሰ እንደመሆኑ መጠን፤ የተንቀሳቃሽ ስልክ አገልግሎት በሚያስገርም ፍጥነት እየተስፋፋ ነው። ይሁንና ከኢንተርኔት ጋር መገናኛው በጣም ውድ ነው ።

«3/4ኛዎቹ ደንበኞች፣ ዝቅተኛ v ገቢ ያላቸው ማለት ነው፤ 50 ከመቶ ወይም ከዚያ በላይ ገንዘባቸውን ለተንቀሳቃሽ የስልክ አገልግሎት ያውላሉ። ከኤኮኖሚ አቅም አኳያ ከታዬ፣ ፍጹም ሊቃጡት የሚገባ አይደለም ። ገንዘባቸውን ልጆቻቸውን ለማስተማርና ለሌሎችም ጠቃሚ ጉዳዮች ሊያውሉት ይችላሉ። ለምሳሌ ያህል ጽሑፎችን ለማተም ሊጠቀሙበት ይችላሉ።»

እስቲቭ ሶንግ በሰሜንና ደቡብ የሥነ ቴክኒክ ትብብር አማካኝነት ሞባይል ስልክን በየትኛውም ቦታ ከኢንተርኔት መረብ ጋር ሊያገናኝ ከሚችል መሣሪኢ ጋር ማዋካድ እንደማያዳግት አሳይተዋል።

«የተሠራው በደቡብ አፍሪቃ ነው። ውጤቱ፤ በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ በዛ ያሉ ጠበብትንም ሆነ ሰዎችን ማርኳል። ይህ ደግሞ በነጻ የመረጃ ሶፍትዌር አገልግሎት- Open Source በኩል ነው ተግባራዊ የሆነው። አንዲት የመገናኛ ጉዳይ አዋቂ ከበርሊን፤ የኮምፒዩተር አካል ቅርጽ አውጪ ከአውስትሬሊያ፣ የኢንተርኔት ስልክ ጉዳይ ዐዋቂ ከአስፓኝና ከአስዊድን፣ እንዲሁም ከቻይና ምሥራቅ ቲሞርና ደቡብ አፍሪቃ ጠበብት ተባባሪዎች በመሆን ተሳትፈዋል። ሥነ ቴክኒክን በማዘዋወሩ ተግባር የተጠቀሰው የሶፍትዌር ዝግጅት በጅቷል። በመሆኑም፣ ዘመናዊና አዲስ ለአፍሪቃ አገልግሎት መስጠት የሚችል መሣሪያ ሊዘጋጅ ይችላል።»

ሴሎ ሌሆንግ የፈለሰፉት ቺሲምባ ፕሮግራም ፣ ለምርምር የአካዳሚ ልውውጥን ለማጠናከር ሰፊ አስተዋጽዖ ያለው ነው። አፍሪቃ የምርምር ውጤት በማቅረብ ረገድ ከዓለም ውስጥ ያለው ድርሻ 0,7 ከመቶ ብቻ ነው። ሁኔታው ከባድ ነው። በነጻ የትምህርት መረጃ ሶፍትዌር አቅርቦት በኩል ብቻ ውጤታማ መሆን ድግሞ የማይቻል ነው። በሰሜኑ ንፍቀ-ክበብ የሚገኙ ታላላቅ ኩባንያዎች ደግሞ በፈጠራ ውጤት ባለቤትነት፣ በንግድ ፈቃድና በመሳሰለው ፣ ሌላው ምንጊዜም የእነርሱ ጥገኛ ሆኖ እንዲቀር ይሻሉ።

«በሚገባ እንደምንታዘበው ማይክሮሶፍትና ዖራክል የየኒቨርስቲዎችን ቤተ-ሙከራና ሶፍትዌር በገንዘብ ድጋፍ መቆጣጠር ይሻሉ። በነገዎቹ የሥራ መሪዎችም ላይ በዚህ ረገድ ተጽእኖ ማድረግ ነው የሚፈልጉት። ታዲያ ተማሪዎች ትምህርታቸውን ሲጨርሱና የአስተዳደር ኀላፊነት ሲሸከሙ፣ የትኛውን ሥነ ቴክኒክ የሚመርጡ ይመስላችኋላ? ገምቱ! የሚቀላቸውን የሚያውቁትን፣ የተማሩበትን ነው የሚሆነው።»

ግራም ነፈሰ ቀኝ ፣ የዕወቀት ተሳታፊ ለመሆን ሰፊ ጥረት ማድረጉ እጅግ ተፈላጊ ነው። እርግጥ ፣ የሥነ-ቴክኒክ ንግድ፣ ተጽእኖ ያሳርፍ ይሆናል። ግን፣ ሁልጊዜ ፣ ሁሉ ነገር በዚያው መልክ ይቀጥላል ማለት አይቻልም።

ተክሌ የኋላ

ሸዋዬ ለገሠ