የደቡብ ሱዳን የሰላም ድርድር ሂደት
ረቡዕ፣ የካቲት 25 2007
ተቀናቃኞቹ ፖለቲከኞች ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለነገ እአአ መጋቢት አምስት፣ 2015 ዓም ያስቀመጠው የጊዜ ገደብ ሳያልፍ በፊት መልስ ላላገኙ ጥያቄዎች መልስ በመሻት የመጨረሻ ስምምነት መድረስ ይጠበቅባቸዋል። ይህን ካላደረጉ ግን ማዕቀብ ሊጣልባቸው እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቿዋል። የደቡብ ሱዳን መንግሥት ማስጠንቀቂያውን ትክክለኛ ያልሆነ ሲል ተቃውሞታል።የደቡብ ሱዳንን የርስ በርስ ጦርነት የማስቆም ዓላማ ያለው የተመድ ማዕቀብ ተግባራዊ ከሆነ ተቃራኒ ውጤት ሊከትል ይችላልም ሲል አስጠንቅቋል ።የደቡብ ሱዳን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ባራንባ ማርያል ቤንጃሚን ፣በደቡብ ሱዳን ላይ የሚጣል ማንኛውም ማዕቀብ የሰላሙን ጥረት ከማጓተቱም በላይ ተራዉን ህዝብም በቀጥታ የሚጎዳ ይሆናል ሲሉ አስጠንቅቀዋል ። ሚኒስትሩ የሰላም እንቅፋቶችን ማስወገድ እንጂ አዲስ ችግር መፍጠር አይገባምም ብለዋል ። ሚኒስትሩ ድርጅቱን ባለመታገሱም ወቅሰዋል።የደቡብ ሱዳን መንግሥት ቃል አቀባይ አትኔ ዌክ አትኔይም የተመድ የማዕቀብ ውሳኔ ከማሳለፍ ይልቅ ሁለቱ ወገኖች እንዲስማሙ መርዳት ይገባው ነበር ብለዋል ።
«የተመድ ፣የደቡብ ሱዳን ተፋላሚ ኃይላት ቡድኖች የሚገኙትበትን ሁኔታ በቅጡ ሳያጤን ይህን ዓይነት የውሳኔ ሃሳብ ማሳለፉ ያሳዝናል ። የደቡብ ሱዳን መንግስት በተደጋጋሚ ለደቡብ ሱዳን ችግር ሰላማዊ መፍትሄ ለመፈለግ ቆርጦ ተነስቷል ።ይህን ነበር የተመድ ከግምት ውስጥ ማስገባት የነበረበት ። ምክንያቱም መንግሥት በደቡብ ሱዳን ሰላም እንዲሰፍን ከምር እየጣረ ነው ።የተመድ በደቡብ ሱዳን ህዝብ ላይ የማዕቀብ ውሳኔ ከማሳለፍ ይልቅ ሁለቱ ወገኖች ስምምነት ላይ እንዲደርሱ ማገዝ ይገባው ነበር ።»
የተመድ የፀጥታው ምክር ቤት ፣የደቡብ ሱዳንን የሰላም ሂደት በሚያደናቅፉ ወገኖች ላይ የጉዞ እገዳ እንዲደረግና ሃብት ንብረታቸውም እንዳይንቀሳቀስ በዩናይትድ ስቴትስ ተረቆ የቀረበለትን የውሳኔ ሃሳብ ያፀደቀው ትናንት ነበር በሙሉ ድምፅ ያፀደቀው ።
ጌታቸው ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
አርያም ተክሌ
ነጋሽ መሀመድ