1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም እግር ኳስ ግጥሚያና ደቡብ አፍሪቃ

ማክሰኞ፣ ግንቦት 3 2002

ሠላም ወረዳ።የትንሸኛዉ ጆርዳን ድል የኬፕታዉን ዕለታዊ ጋዜጣ የፊት ገፅ ታሪክ ሆነ።ዳኒም ለታናሽ ወንድማቸዉ እሩቅ አልነበሩም።

https://p.dw.com/p/NLSR
ደርባን እግር ኳስምስል DW/Arnulf Boettcher

11 05 10

የዘንድሮዉ የአለም እግር ኳስ የዋንጫ ግጥሚያ በመጪዉ ወር ልክ የዛሬን ዕለት ደቡብ አፍሪቃ ዉስጥ ይጀመራል።አለም አቀፉ ትልቅ የእግር ኳስ ግጥሚያ አፍሪቃ ዉስጥ ሲስተናገድ የዘንድሮዉ የመጀመሪያዉ ነዉ-የሚሆነዉ።ለግጥሚያዉ የሚደረገዉ ዝግጅት የአፍሪቃን በተለይ ደግሞ የደቡብ አፍሪቃን ሁለት የተራራቀ ገፅ የሚያሳይ ነዉ።በቅርቡ ደቡባ አፍሪቃን ጎብኝቶ የተመለሰዉ ሉድገር ሻዶምስኪ እንደፃፈዉ ደግሞ ሁለቱ ጆርዳኖች በርግጥ የደቡብ አፍሪቃን ሁለት ገፅታ አመልካቻቾ ናቸዉ።የሉድገርን ዘገባ ነጋሽ መሐመድ አጠናቅሮታል።

«የደቡብ አፍሪቃ-ንጉስ» ይሏቸዋል-አድናቂ አሞካሺያቸዉ-ዳኒ ጆርዳንን። የደቡብ አፍሪቃ የስፖርት አድራጊ ፈጣሪ፥የዘንድሮዉ የአለም እግር ኳስ ግጥሚያ ደግሞ ገፅ-የሕዝብ አይንና ጆሮም ናቸዉ። ከእግር ኳሱ አለም አቀፍ ዝግጅት ዉጣ ዉረድ ብዙ ርቀት ላይ ባለዉ-ሌላ ሕይወት መሐል ደግሞ አንድ ሰዉ አለ።ሉቬሌይ ጆርዳን።የማሕበራዊ ጉዳይ ሰራተኛ በመሆናቸዉ የእለት ከእለት ምግባር ኑሯቸዉ ከአደንዛዥ እፅ ወሳጆች፥ ከሰካራሞች፥ ከወጣት ሥራ አጦች፥ ከተደፈሩ ሴቶች ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነዉ።

ሰዎቹ-በርግጥ የሩቅ ለሩቅ እዉነታ፣ የሁለት አለም ሁለት ሰዉ ናቸዉ።ግን ደግሞ-የአንድ ወላጆች ዉልድ፥የአንድ ሐገር ዜጎች፥ የአንድ ሕብረተሰብ ግኝት ናቸዉ።ደቡብ አፍሪቃዊ።ሁለትም አንድሞቹ-እግር ኳስ በአመፅ-ግጭት ሁከት የተሞላዉን የደቡብ አፍሪቃን ማሕበረሰብ ለማሻሻል ትንሽ ግን ጥሩ እርምጃ ነዉ-የሚል አንድ እምነት አላቸዉ።

«ማጅራት መቺዎቹ ገና ከጅምሩ አንድ ላይ ሆነን ኳስ እንጫወት ነበር-ያሉት።ይሕ እንግዴሕ የሚያስተባብር የሥፖርት ልዩ ሚስጥር ነበር።»
ይላሉ ዳኒ ጆርዳን።ቀልጣፋ ናቸዉ።ከተፎ-እና ደግሞ ዝነኛ።ለስለስ-ረጋ ያሉት ሉቬሊን ጆርዳን የእግር ኳሱ መሰናዶ-የሚያጣድፋቸዉን ዝነኛ ወንድማቸዉን ለማግኘት ብዙ ጊዜ ሞክረዉ ነበር።ትልቁ ሰዉዬ ሥልክ ለመመለስ እንኳን ጊዜ የላቸዉም።
በ1990ዎቹ አጋማሽ (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ግን የሁለቱ ወንድማቾች ሁለትነት ትንሽ አንድነቱ ትልቅ ነበር።የሽቦ-መስመሩ ግንኙነትም ቅርብ።በደቡብ አፍሪቃ የመጀመሪያዉ ሁሉን ዘር-አቀፍ ምርጫ በ1994 ከመደረጉ ቀደም ብሎ-የሌቨንደር ሒል መንደር እንደ መላዉ ሐገሪቱ ሁሉ ከእርስ በርስ ጦርነት አፋፍ ላይ ነበረች።

WM Städte und Stadien der Fußball WM in Südafrika Bloemfontein
ከስታዲዮሞቹ አንዱምስል AP

ማጅራት መቺዎች በየዕለቱ የሚገድሉት ሰዉ ቁጥር-እየናረ፥ ሥጋቱ እያየለ፥ ፍጥጫዉ እየከረረ የሐገሪቱ ጦር ቃታ ለመሳብ-በተጠንቀቅ በቆመበት በዚያ ወቅት ታንሽ ወንድምዬዉ መላ መቱ። ኳስ።በሁለት ስም የሚጠሩትን ሐይለኛ ማጅራት መቺዎች እሁለት አቧድነዉ እግር ኳስ አጋጠሟቸዉ።ሽጉጥ የታጠቁት ሳይቀሩ-አንድም ኳስ ተጫዋች አለያም ተመልካች ሆኑ።

ሠላም ወረዳ።የትንሸኛዉ ጆርዳን ድል የኬፕታዉን ዕለታዊ ጋዜጣ የፊት ገፅ ታሪክ ሆነ።ዳኒም ለታናሽ ወንድማቸዉ እሩቅ አልነበሩም።

«ደወልኩለት እና ሥማ ይሕ ነዉ የሆነዉ አልኩት።የመጀመሪያዉን መደበኛ ያልሆነ የእግር ኳስ ማሕበረን መሠረትን።ላቭደር ሒል የእግር ኳስ ማሕበርን።እሱ ደግሞ ማሕበሩ ሕጋዊ እዉቅናና መዋቅር እንዲኖረዉ ረዳን።»

ዘንድሮ አስራ-ስድስት አመት አለፈዉ።ሕይወት የሚያጠፋዉ ሁከት ዛሬ በርግጥ በእጅጉ ቀንሷል። ሰማን-አምስት ሺሕ ለሚገመዉ ለላቬንደር ሒል ነዋሪ ግን ሕይወት ብዙም አልተቀየረችም።ከወጣት ነዋሪዎችዋ ሰማንያ-አምስት ከመቶዉ ሥራ አጥ ነዉ።መንደሪቱ የድሕረ ዘር መድሎ ሥርዓት ደቡብ አፍሪቃ ችግሮች ጎልተዉ ከሚታዩባቸዉ አካባቢዎች አንዷ ናት፥-የአልኮል ሱሠኞች፥ የሚደፈሩ ሴቶችና ሕፃናት የበዙባት ሠፈር።

እንደ ጥቅል ደቡብ አፍሪቃ ማሕበረሰብ-የቀለም፥ የሐብት፥ የሥልጣን ክፍተት-ልዩነት ሁሉ የሁለቱ ወንድማማቾች-ርቀት፥ወይም ሁለትነት በጣም ሠፍቷል።በጭካኔ የተሞላዉ የደቡብ አፍሪቃ ማሕበረሰብ ባንድ ነገር-ይሻሻላል በሚል እምነት-ራዕያቸዉ ግን ሁለቱ ጆርዳኖች አንድ ናቸዉ።ደቡብ አፍሪቃዉያንም።ያ አንድ ነገር።
እግር ኳስ።ልጆቹ ከአደንዛዥ ይልቅ የሊቨር ፑል መለያን አጥልቀዉ፥ለዘንድሮዉ የአለም እግር ኳስ ግጥሚያ በተዘጋጀዉ ቀለም ያሸበረቀዉን ኳስ ይጠልዛሉ።ሉቬሌይ ጆርዳን ረክተዋል።
«ይሕንን ቅምጥ ችሎታ በበጎ ጎኑ ማዳባር አለብን።እነሱ (ልጆቹ) መጥፎ እጅ ላይ እንዳይወድቁ የመንከባከብ እና ዋስትና የመስጠት ሐላፊነት አለብን።»

Südafrika Fußball Nationalmannschaft
የደ/አ ብሔራዊ ቡድንምስል Picture-alliance/dpa

ሉድገር ሻዶምስኪ

ነጋሽ መሐመድ

ሒሩት መለሰ