1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና

ሰኞ፣ መጋቢት 3 2004

ቱርክ-ኢስታምቡል ውስጥ የተካሄደው የዓለም የአዳራሽ ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ትናንት ለኢትዮጵያም ስኬታማ በነበረ ውጤት ተጠናቋል።

https://p.dw.com/p/14JOU
ምስል AP

ቱርክ-ኢስታምቡል ውስጥ የተካሄደው የዓለም የአዳራሽ ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ትናንት ለኢትዮጵያም ስኬታማ በነበረ ውጤት ተጠናቋል። በውድድሩ ዩ-ኤስ-አሜሪካ አሥር ወርቅ ሜዳሊያዎችን በማግኘት አሸናፊ ስትሆን ብሪታኒያም በሁለት ወርቅ፣ ሶሥት ብርና በአራት ናሃስ ሁለተኛ ውጥታለች። ኢትዮጵያ ደግሞ በሁለት ወርቅ፣ አንድ በርና ሁለት ናሃስ ኬንያን ከኋላዋ በማስቀረት ሶሥተኛ ሆናለች።

 መሐመድ አማን በ 800 ሜትርና ገንዘቤ ዲባባ በ 1500 ሜትር ሩጫ በየፊናቸው ለወርቅ ተሸላሚነት ሲበቁ መሠረት ድፋርና ገለቴ ቡርቃም በ 3000 ሜትር ሁለተኛና ሶሥተኛ በመውጣት ግሩም ወጤት አስመዝግበዋል። ስለ ኢትዮጵያ አትሌቶች ውጤትና ጥሩ ተሳትፎ ውድድሩን በቅርብ ስትከታተል የሰነበተችውን ጋዜጠኛ ሃይማኖት ጥሩነህንና የ 800 ሜትር አሸናፊውን መሐመድ አማንን ዛሬ ረፋዱ ላይ ከኢስታምቡል በስልክ አነጋግሬ ነበር፤ ያድምጡ!  

የተቀሩትን ውጤቶች በጥቂቱ ለመጠቃቀስ ያህል ከኬንያ የመነጨው አሜሪካዊ በርናርድ ላጋት ሁለት ኬንያውያንን አስከትሎ አንደኛ ሲወጣ ደጀን ገ/መስቀል አምሥተኛ፤ እንዲሁም የኔው አላምረው ዘጠነኛ በመሆን ሩጫውን ፈጽመዋል። ከዚሁ ሌላ ፋንቱ ማጊሶ በ 800 ሜትር አራተኛ በመውጣት ጥሩ ወጤት ስታስመዘግብ በተረፈ በአጭር ርቀት ሩጫና የዝላይ ስፖርት የአሜሪካ አትሌቶች በኦሎምፒኩ ዓመት አይለው ታይተዋል።

እግር ኳስ

Fussball 1. Bundesliga 25. Spieltag, FC Bayern Muenchen gegen TSG 1899 Hoffenheim in Allianz-Arena Muenchen
ምስል picture alliance/augenklick/GES

በስፓኝ ፕሪሜራ ዲቪዚዮን የሮናልዶና የሜሲ የጎል ፌስታ ባለበት ሲቀጥል እያንዳንዳቸው ሁለት ጎሎችን በማስቆጠር የየክለቦቻቸው ድል ዋስትና ሆነዋል። ሬያል ማድሪድ ቤቲስን 3-2 አሸንፎ በአሥር ነጥቦች ልዩነት መምራቱን ሲቀጥል ባርሤሎናም ሣንታንዴርን  2-0 በመርታት ሁለተኛ ነው። በእንግሊዝ ፕሬሚየር ሊግ ማነቼስተር ሢቲይ በመሸነፉ ተፎካካሪው ማነቼስተር ዩናይትድ ካለፈው ጥቅምት ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ አመራሩን ሊይዝ በቅቷል።                                                                                        

በአልቢዮን ላይ ሁለት ጎሎች በማስቆጠር ለማኒዩ የድል ዋስትና የሆነው ዌይን ሩኒይ ነበር። በጀርመን ቡንደስሊጋም የቀደምቱ ዶርትሙንድ ከፍራይቡርግ ባደረገው ግጥሚያ በእኩል ለእኩል ውጤት መወሰን ለባየርን በጅቶታል። ባየርን ሆፈንሃይምን 7-1 ቀጥቶ በመሸኘት ከዶርትሙንድ ጋር ያለውን ልዩነት ወደ አምሥት ሲያጠብ ድሉ በነገው ምሽት 1-0 አሸንፎት ከነበረው ከባዝል ጋር ለሚያካሂደው የአውሮፓ ሻምፒዮና የመልስ ግጥሚያም ብርታት እንደሚሰጠው ዕምነት አለ።

የአውሮፓን ሻምፒዮና ሊጋን ካነሣን ካለፈው ሣምንት የተቀሩት ለሩብ ፍጻሜ የሚካሄዱት የመልስ ግጥሚያዎች ነገና ከነገ በስቲያ ይደረጋሉ። በነገው ምሽት ኢንተር ሚላን ከኦላምፒክ ሊዮንና የጀርመኑ ባየርን ሙንሺን ከባዝል የሚጋጠሙ ሲሆን በማግሥቱ ረቡዕ ደግሞ ቼልሢይ ከናፖሊና ሬያል ማድሪድ ከሞስኮ ይገናኛሉ። ባለፈው ሣምንት ቤንፊካ ሊዝበን፣ ኤሲ ሚላን፣ አፓል ኒኮዚያና ባርሤሎና ወደ ሩብ ፍጻሜው መሻገራቸው አይዘነጋም።

መሥፍን መኮንን