የኮሪያ ልሳነ ምድር-ሠላምና ጦርነት
ሰኞ፣ ሚያዝያ 7 2005
ምላጭ አልተሳበም።ሰሜን ደቡብ የተፋጠጠዉ፣ ኒኩሌር ቦምብ የታጠቀዉ ከሚሊዮን በላይ ጦር ግን ታንክ-ሚሳየል፣ቦምብ፣ መትረየሱን እንዳቀባበለ ነዉ።የኮሪያ ልሳነ ምድር።ሠላም ይዉረድ የማይልለት ዓለም የለም።የፒዮንግዮንግ፣ የሶል ዋሽግተኖች የዉጊያ ዘመቻ፣ ዝግጅቱ ፉከራ-ቀረርቶዉ ግን እንደጋመ ነዉ።ዉጊያ ከተጫረ፣ ዓለም እስከ ዛሬ ከሚያቃቸዉ ጦርነቶች ሁሉ አስከፊ የሚያደርገዉ የኒኩሌር ቦምብ ጦርነት ይሆናል መናሉ ነዉ።ጅምላ ጨረሹ ቦምብ የትልቅ ሥጋት ፍርሐት ምንጭ እንደሆነ ሁሉ፣ ዉጊያዉ እንዳይጫር ማገጃ ሰበብ ሊሆንም ይችላል። ይቃረናል። እንዴት ?
ዩናይትድ ስቴትስ ከ1945 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) ደቡብ ኮሪያ ያሠፈረችዉን ጦር እንዲያጠናክር አዲስ ጦር እና የጦር መሳሪያ ብታዘመት፥ባለሥልጣናቷ ሰሜን ኮሪያን ለመዉጋት ቢዝቱ ቢያስጠነቅቁ፥ የሶል ትኪዮ መሪዎች ዛቻ፥ ፉከራዉን ቢያዳምቁ፥ የፒዮንግዮግ ገዢዎች ቢያቅራሩ ከ1950 ጀምሮ «ቴክኒካዊ» ከሚባለዉ ጦርነት ላይ ናቸዉና አያስደንቅም። ባለጉዳይ ናቸዉ።
የሩሲያዉ ፕሬዝዳት ቭላድሚር ፑቱን ባለፈዉ ሳምንት ጀርመንን የጎበኙት፥ የጀርመንዋ መራሒተ፥ መንግሥት ወይዘሮ አንጌላ ሜርክል ፑቲንን የጋበዙትም ሐኑፈር-ሰሜን ጀርመን የሚታየዉን የኢንዱስትሪ ትርዒት ሁለቱ ሐገራት በጋራ በመዛጋጀታቸዉ ነበር።የሁለቱ ሐያል፥ ሐብታም ሐገራት መሪዎች ከሐኖፈሩ የኢንዱስትሪ ትርዒት እኩል የኮሪያ ልሳነ-ምድሩን አስጊ የዉጊያ ትርዒት ጉዳያቸዉ አለማድረግ ግን አይችሉም ነበር።
«የኮሪያን የኑክሌር መርሐ-ግብር በተመለከተ የኛ አቋም በግልፅ የታወቀ ነዉ።የጅምላ ጨረሻ ጦር መሳሪያ ሥርጭትን እንቃወማለን።ከማንኛዉም ነገር በላይ የኮሪያ ልሳነ-ምድር ከኑክሌር ጦር መሳሪያ መፅዳት አለበት የሚለዉን ሐሳብ እንደግፋለን።በመጨረሻም ለጥያቄዉ በቀጥታ መልስ ለመስጠት ያሕል፥ የኮሪያ ልሳነ ምድር ዉጥረት መናሩ ያሳስበናል።ምክንያቱም ጎረቤቶቻችን ናቸዉ።እንዲያዉ፥ አያድርስ እና የሆነ ነገር ቢፈጠር እስካሁን በጣም የሚታወቀዉ የቼርኖቤል (የኑክሌር ጣቢያ ፍንዳታ) ያደረሰዉ ጥፋት አሁን ሊደርስ ከሚችለዉ ጥፋት ጋር ሲነፃፀር ተረት ተረት ነዉ።»
ፕሬዝዳት ቭላድሚር ፑቲን።
ሞስኮ የመስጋት፥ ማሰቧ ምክንያት የፒዮንግዮንግ ኮሚንስታዊ ሥርዓት የቀድሞ መሥራች፥ የአሁን የሩቅም ቢሆን ወዳጅ መሆንዋ፥ ፑቲን ካሉት ከጉርብትናዉ፥ ከቼርኖቤሉ ጥፋት ጋር በሰወስተኝነት የሚደረብ ነዉ።
የጀርመንዋ መራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልም ከሐኖፈሩ ትርዒት በላይ የኮሪያ ልሳነ-ምድርን ዉጥረት ልዩ ትክረታቸዉ ያደረጉበት የዩናይትድ ስቴትስ ወዳጅ ሐገር መሪ በመሆናቸዉ ብቻ አይደለም።ከሚፈራዉ አጥፊ ጦርነት አትራፊ አለመኖሩን ሥላወቁት እንጂ፥-
«እኔ በበኩሌ አሁንም ዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ በጋራ ለመስራት የሚስማማበትና የጋራ አቋም የሚይዝበት ሁኔታ አስፈላጊ ነዉ ባይ ነኝ።ከዚሕ አኳያ የሩሲያ ሚና፥ በርግጥ የቻይና ሚናም ልዩ ትርጉም አለዉ።እንደሚመስለኝ ሰሜን ኮሪያ ዓለም አቀፍ ግዴታዎቿን ማክበር አለባት በሚለዉ ሐሳብ ሁላችንም «መሠረተ-ሠፊ» የጋራ አቋምና አላማ አለን።»
በዚያዉ ባለፈዉ ሳምንት ለንደን-ብሪታንያ የተሰበሰቡት የሥምንቱ በኢንዱስትሪ የበለፀጉት ሐገራት ዉጪ ጉዳይ ሚንስትሮች፥ ደብሊን-አየር ላንድ የተሰበሰቡት የአዉሮጳ ሕብረት የገንዘብ ሚንስትሮችም ሥለ ሶሪያ ጦርነት፥ ሥለ አዉሮጳ ኪሳራ፥ ሥለ ሌላም መምከር መነጋገራቸዉ አልቀረም።ትልቁ ርዕስ-ትኩረታቸዉ ግን የኮሪያ ልሳነ ምድር ዉጥረት ነበር።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ ፓን ጊ ሙንም የኮሪያ ልሳነ-ምድር ዉጥረትን በልዩ ትኩረት እንዲከታተሉት ከደቡብ ኮሪያዊነታቸዉ በላይ የዓለም አቀፉ ማሕበር መሪነታቸዉ ግድ ብሏቸዋል።
«ዉጥረቱ አሁን ከደረሰበት በጣም አደገኛ ደረጃ መድረሱ እንደ አንድ ኮሪያዊ ዜጋ በጣም ያሳስበኛል፥ ያስጨንቀኛልም።በተሳሳተ ሥሌት ወይም በተሳሳ ዉሳኔ ትንሽ ችግር ቢፈጠር ሊቆጣጠሩት የማይቻል ትልቅ (ጥፋት) ያስከትላል።ለዚሕም ነዉ፥-የዲሞክራቲክ ሕዝባዊት ሪፐብሊክ ኮሪያን ባለሥልጣናት ከጠብ አጫሪነት ቀረሮቷቸዉ እንዲታቀቡ የማሳስበዉ።የኮሪያ ልሳነ-ምድርና አካባቢዉ የሚመለከታቸዉ ሐገራትም በሰሜን ኮሪያ ላይ ያላቸዉን ተፅዕኖ (ችግሩን ለማቃለል) እንዲጠቀሙበት የማሳስበዉም ለዚሕ ነዉ።»
ቬልትሁንገር ሒልፈ የተሰየኘዉ የጀርመን ግብረ ሠናይ ድርጅት የተቸገሩና የተራቡ ሰዎችን ከመርዳት ባለፍ የዓለምን ፖለቲካዊ፥ ወታደራዊ፥ዲፕሎማሲያዊ ዕዉነት፥ ሒደት የመዘወር አቅም አላማም የለዉም።ሰሜን ኮሪያ ዉስጥ ላለፉት አስራ-አምስት ዓመታት ርዳታ ሲያከፋፍል ነዉ-የኖረዉ።
ዘንድሮ በዚሕ ሰሞን ግን በአስራ-አምስት አመት ዉስጥ አይቶት የማያዉቀዉ ፈተና ገጥሞታል። የድርጅቱ ሐላፊ ጌርሐርድ ኡርማሐር በቀደም እንዳሉት እሳቸዉም፥ ባልደረቦቻቸዉም በኮሪያ ልሳነ ምድር ወታደራዊ ፍጥጫ ሒደት፥ ንረት ላይ እንዳፈጠጡ ነዉ።
«ሁኔታዉን ከምር ነዉ የምናየዉ። የደረሰበትን ደረጃ ዕለት በዕለት እየተከታተልን፥ ሥራችንን መቀጠል አለመቀጠላችንን ለመወሰን እየመረመርንም ነዉ።»
የተቀረዉ ዓለም ችግር፥ ፍላጎት፥ ትኩረትም ለየቅል፥ አንዳዴም ተቃራኒ ሊሆን ይችላል።ይሁንና ካለፈዉ ሰኞ እስከ ዛሬ ብቻ የሐኖፈር ጎብኚ-አስጎብኚዎችን፥ የለንደን፥ ደብሊን ተሰብሳቢዎችን፥ የኒዮርክ ዲፕሎማቶችን፥ የበርሊን፥ ሲዊዘርላንድ ርዳታ ሰጪዎችን በሚያሳስብ፥ በሚያሰጋዉ ጉዳይ አለመስጋት፥ አለመጨነቅም አይችልም።
ያቺ ሐገር።ከጠላቶችዋ ግዘፍትና ብዛት ጋር ሲነፃፀር የትንሾች ትንሽ ነች።ሰሜን ኮሪያ። በሕዝብ ብዛት ከቀንደኛ ጠላቷ ከዩናይትድ ስቴትስ፥ ወይም ከመለስተኛ ጠላቷ ከጃፓን ቀርቶ ከቅርብ ጠላቷ ከደቡብ ኮሪያ ጋር ሲነፃፀር እንኳን በግማሽ ያነሰ ነዉ።ሃያ-አምስት ሚሊዮን።አጠቃላይ አመታዊ ገቢዋ ከአሜሪካዉ ጄኔራል ሞተርስ፥ ከጃፓኑ ቶዮቷ ወይም ከደቡብ ኮሪያዉ ሳምሱንሱግ ኩባንያ ገቢ ያነሰ ነዉ።
የሕዝብ ብዛት፥ የቆዳ ሥፋት፥ የሐብት መጠን ትንሽነት ብቻ የጉልበት ደከማነት ቢሆን ኖሮ፥ የዓለም ዘዋሪዎች ኪም ጆንግ ኡንን እንደ ሳዳም ሁሴን ባደባባይ ለማንጠልጠል፥ ወይም እንደ ሙዓመር ቃዛፊ አዉላላ ሜዳ ላይ ለማስረሸን አፍታ ባልፈጀባቸዉ ነበር።ግን የዋይት ሐዉሱ ቃል አቀባይ ጄን ካርኔይ በቀደም እንዳሉት የቆዳ ሥፋት፥ የሕዝብ ቁጥር፥ የሐብት መጠን ትንሽ ትልቅነት አይደለም-ጉዳዩ።
«ሰሜን ኮሪያዎች የኑክሌር ጦር መሳሪያ ሞክረዋል።የተወሰነ የሚሳዬል ተክኖሎጂም አዳብረዋል። ያላደረጉት ነገር የኑክሌር ጦር ቦምብ ማወንጨፍ የሚችል ሚሳዬል መሥራት አለመስራታቸዉን በግልፅ አለማሳየታቸዉ ነዉ።ያም ሆኖ የገቡትን ቃል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ጥሰዉ እነዚሕን መሳሪያዎች የመስራት መርሐ-ግብራቸዉን መቀጠላቸዉ ምንም አያጠያይቅም።»
የትንሺቱ ኮሚንስታዊት ሐገር ትንሽ ሚሳዬል፥ ኖዶንግ ፥ደቡብ ኮሪያ የሚገኝ ኢላማዉን ለመምታት በቂ ነዉ።አንድ ሺሕ ኪሎሜትር ይምዘገዘጋል።ቴዬፖዶግ-አንድ፥የጃፓን ግዛቶችን ለማንቀርቀብ በቂ ነዉ።ሁለት ሺሕ ሁለት መቶ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ኢላማዉን ይመታል።ሰዎተኛዉን ሙስዶን አሉት።አራት ሺሕ ኪሎ ሜትር-ይምዘገዘጋል።
ኪም ጂንግ ኡን ካዘዙ፥ ቴዬፖዶንግ-ሁለት የተሰኘ ሚሳዬላቸዉ ቁልቁል ወደ ደቡብ ቢተኮስ የአዉስትሬሊያ፥ ሽቅብ ወደ ሰሜን ቢያወነጭፉት የዩናይትድ ስቴትስን ግዛቶች ያደባያል።ስድስት ሺሕ ኪሎሜትር ይምዘገዘጋል።
ኑክሌርም ታጥቃለች።ከአንድ ሚሊዮን በላይ ወታደርም አሰልፋለች።ይሕ ነዉ-የዓለም ሥጋት።ይሕ ነዉ ሐያላኑ ዓለም እንደ ሰርቢያ፥ እንደ ኢራቅ፥ እንደ ሊቢያ፥ እንደ አፍቃኒስታን፥ እንደ ማሊ፥ እንደ ሌላዉም ሐይል ጡንቻቸዉን እንዳይፈትሹ ያገደዉ።
እርግጥ ነዉ ሳዳም ሁሴን ባደባባይ ማንጠልጠል፥ ሙዓመር ቃዛፊን በጠረራ ፀሐይ ማሽረሸን የተቻለዉ ሁለቱም የየኑክሌር፥ ወይም የየጅምላ ጨራሽ ጦር መሳሪያ መርሐ-ግብራቸዉን በየራሳቸዉ እጅ እንዲያጠፉ ሐያሉ ዓለም ካግባባ፥ ካስፈራራና ካስጠፋቸዉ በኋላ ነዉ።
በ1998 የደቡብ ኮሪያን የፕሬዝዳትነት ሥልጣን የያዙት ኪም ዴ ጁንግ እና የያኔዉ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳት ቢል ክሊተን መስተዳድሮች ከፒዮንግ ገዢዎች ጋር ያደረጉት ድርድር ኪም ጆንግ ኢልን እንደ ሳዳም፥ አለያም እንደ ቃዛፊ ክላሺንኮቭ ታቅፈዉ እንዲቀሩ ያለመ-ሊሆን፥ ወይም በይፋ እንደተነገረዉ ኮሪያዎችን በሰላም ለማዋሐድ ያለመ ሊሆን ይችላል።
የሰሜን ኮሪያን የኑክሌር መርሐ-ግብር በእንጩጩ ለማስቀረት ግን አፋፍ ላይ ደርሶ ነበር።ኪም የፀሐይ ነፀብራቅ፥ ያሉት የሠላም መርሕ፥ ቢል ክሊንተን የመሩት የስድስትዮሽ ድርድር የሰሜን ኮሪያን የኑክሌር መርሐ-ግብር አስቁሞ ነበር። የኮሪያ መሪዎችን ፊትለፊት አገናኝቶ ነበር።የአሜሪካ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትርን ፒዮንግዮንግ፥ የሰሜን ኮሪያ ምክትል መሪን ዋሽንግተንን አስጎብኝቶ ነበር።
በሁለት ሺሕ አንድ ቢል ክሊንተንን የተኩት ፕሬዝዳት ጆርጅ ደብሊዉ ቡሽ፥ አል-ቃኢዳ ባደረሰዉ ጥቃት ሰበብ የመለዉ ዓለምን ሠላማዊ ሒደት፥ የድርድር ዉይይት ጅምር ዉጤትን፥ የምጣኔ ሐብት እድገትንም ግራቀኝ ሲያላጉት ኮሪያ ልሳነ-ምድርድር ላይ የፈነጠቀዉን የሰላም ጭላንጭልንም መረጉት።ኪም ጆንግ ኢሊም በተደፈናዉ ጭለማ መሐል ኑክሌር መታጠቃቸዉን አወጁ።2006። በሰወስተኛዉ ዓመት ደገሙት።ልጃቸዉ ኪም ጆንግ ኡን ዘንድሮ አሠለሱት።
አስጊዉ ጦር መሳሪያ የአስከፊ ፍጅት ምክንያት የመሆኑን ያሕል አስጊዉን ጦርነት ለማስቀረትም ሰበብ ሊሆን ይችላል።ፕሬዝዳንት ሐሪ ኤስ ትሩማን በኮሪያዉ ልሳነ-ምድር ጦርነት ወቅት ቤጂንግን ወይም ፒዮንግዮንግን ዳግማዊ ሔሮሺማ ወይም ናጋሳኪ ለማድረግ ከመዛት መፎከር ባለፍ አዉዳሚዉን ቦምብ ያልስፈነዱት ቢያንስ ሞስኮዎች ጋ ተመሳሳዩ እሳት መኖሩን ሥለተገነዘቡት ነበር።
ዩናይትድ ስቴትስ እና ሶቬት ሕብረት ከበርሊን እስከ ኩባ ሚሳዬል እያቀባበሉ ከመተኮስ የታቀቡት ሁለቱም ኑክሌር በመታጠቃቸዉ ነበር።«እዚያም ቤት እሳት አለ» እንዲል አበሻ።ሕንድና ፓኪስታን ሑለት መንግሥት ባቆሙ ማግሥት ከ1947 ጀምረዉ በ1965፥በ1971 በገጠሙት ዉጊያ ተላልቀዋል።
ኑክሌር ከታጠቁ በሕዋላ በ1999 መዋጋታቸዉም አልቀረም።የኋለኛዉ ዉጊያ ግን ካሺሚር ላይ ከመኮራኮም ባለፍ እንደቀዳሚዎቹ የሚሊዮኖችን ሕይወት ወደሚያረግፍ ሙሉ ጦርነት አልናረም። የመጨረሻዉ ዉጊያ ወደ ሙሉ ጦርነት ከመጋም ያቀበዉ፥ የሐያሉ ዓለም ጫና፥ የሁለቱ ሐገራት አቅም፥ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዲፕሎማሲ ነዉ የሚሉ አሉ።እነዚሕ ሁሉ ግን በቀዳሚዎቹ ጦርነቶች ወቅት ነበሩ።አዲሱ ነገር ሁለቱም ኑክሌር መታጠቃቸዉ፥ አጥፊዉን ቦምብ መተኮስ አጥፍቶ መጥፋት መሆኑን በመረዳታቸዉ ነዉ።
በኮሪያ ልሳነ-ምድር የተቀባበለዉን መሳሪያ፥ ብልሕ አመራር ካገኘ የኑክሌር ቦምብ መታጠቅ እንዳይተኮስ ሊያስቀረዉ ይችላል።ከሳምት በፊት ሶል ድረስ ሔደዉ ሰሜን ኮሪያን ለመዉጋት የዛቱ የፎከሩት የዩናይትድ ስቴትስ ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ጆን ኬሪ ባለፈዉ ቅዳሜ ቤጂንግ ድረስ ሔደዉ የቻይኖችን አማላጅነት መጠየቃቸዉ የትልቂቱን ሐገር ትልቅ ብስለት ጠቋሚ ነዉ።
«በዚያ ዉይይት ዉጤት መሠረት እኛ፥ ዩናይትድ ስቴትስ እና ቻይና የኮሪያ ልሳነ ምድርን በሰላማዊ መንገድ ከኑክሌር ማፅዳት አስፈላጊ መሆኑን የጋራ ትኩረት ለመስጠት ችለናል።»
በሰሜን ኮሪያ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ከምታሳርፈዉ ከቻይና ዉጪ ጉዳይ ሚንስትር ከያንግ ጂቺይ የተሰማዉ አፀፋም የሩቅም ቢሆን የሰላም ተስፋ ፈንጣቂ ነዉ።
«ጉዳዩ በድርድር እና በምክክር በሰላማዊ መንገድ መያዝ አለበት በሚለዉ አቋማችን እንደፀናን ነዉ።የኮሪያን የኑክሌር ጉዳይ በተገቢዉ መንገድ መያዝ የሁሉምንም ወገኖች ፍላጎት የሚያረካ ነዉ።የሁሉም ወገን የጋራ ሐላፊነትም ነዉ።»
ሰሜን ኮሪያ ዛሬ ተከብሮ ለዋለዉ ለሀገሪቱ የመጀመሪያ መሪ ለኪም ኢል ሱንግ አንድ መቶ-አንደኛ ዓመት ልደት ኑክሌር አወንጫፊ ሚሳዬል ለሙከራ ለመተኮስ ፎክራ ነበር።እስካሁን በደረሰን ዘገባ መሠረት ግን ከርችት፥ ችቦ በስተቀር ሚሳዬል አልተኮሰችም።በርግጥ ካልተኮሰች፥ የቻይኖች ተፅዕኖ፥ የአሜሪካኖች ዲፕሎማሲ ያንዣበበዉን የጦርነት ሥጋት ለመግፈፍ-በተገቢዉ ጎዳና አንድ የማለቱ ምልክት ነዉ።እስከ መቼ አናዉቅም።ለዛሬ ግን ነጋሽ መሐመድ ነኝ።በዚሑ ይብቃን።
ነጋሽ መሐመድ
ሒሩት መለሠ