የኦሕዴድ ዉሳኔ፤ ድጋፍና ተቃዉሞዉ
ሐሙስ፣ ጥር 5 2008የኦሮሚያ መስተዳድር ማብራሪያ
የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) የአዲስ አበባና የአጎራባቾችዋ የኦሮሞ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን የተባለዉ ዕቅድ እንዲቆም የወሰነዉ የኦሮሞ ሕዝብ ዕቅዱን በመቃወሙ እንደሆነ የኦሮሚያ መስተዳድር አስታወቀ።በኦሮሚያ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሐላፊ እንደሚሉት ዕቅዱን ሕዝቡ በእሳቸዉ አገላለጥ «ከጫፍ እስከ ጫፍ» ተቃዉሞታል።ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር ሐላፊዉን አነጋግሮ ያጠናቀረዉ ዘገባ አለ።
----------------------------------------------------------------------------------------
የመንግሥትና የተቃዋሚዎች አስተያየት
የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲ ድርጅት «ኦሕዴድ» ማዕከላዊ ኮሚቴ የአዲስ አበባና የኦሮምያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን እንዲቆም ያሳለፈውን ዉሳኔ እንደሚያከብር የኢትዮጵያ መንግሥት አስታወቀ። ማስተር ፕላኑ መቆሙ ቢገለጽም ተቃዋሚዎች ሙሉ በሙሉ መሰረዙን በጥርጣሪ ነዉ የተመለከቱት። በማስተር ፕላኑ ሰበብ በተነሳው ተቃውሞ በሁለት ወራት ጊዜ ዉስጥ ወደ 140 ሰዎች እንደተገደሉ ና በርካቶች እንደቆሰሉ የኦሮሞ ፌደራላዊ ኮንግረስ በምህፃሩ ኦፌኮ አስታውቋል ። አዜብ ታደሰ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ሚኒስትር አቶ ጌታቸዉ ረዳንና ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችን አነጋግራ ዘገባ አጠናቅራለች።
-----------------------------------------------------------------
አሜሪካ የሚኖረዉ የኦሮሞ ማሕበረሰብ
የኦሮሚያ ገዢ ፓርቲ የኦሮሞ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦሕዴድ) ያሳለፈዉ ዉሳኔ ዩናይትድ ስቴትስ ከሚኖሩ የኦሮሞ ማሕበረሰብ አባላት አወንታዊ፤ አሉታዊም ምላሽ ነዉ የገጠመዉ።የዋሽግተን ዲሲዉ ወኪላችን ናትናኤል ወልዴ ካነጋገራቸዉ አንዱ እንዳሉት ኦሕዴድ ዕቅዱ እንዲቆም መወሰኑ ለሕዝብ ተቃዉሞ መንበርከኩን የሚያረጋግጥ ነዉ።ይሁንና ዉሳኔዉን የዘገየ ብለዉታል-እኚሁ አስተያየት ሰጪ።ሌሎች ግን ከአንድ ወር በላይ በዘለቀዉ ግጭት ለገተገደሉና ለቆሰሉት ካሳ የሚያሰጥ፤ ገዳይ አቁሳዮችን ለፍርድ የሚያቀርብ ኮሚሽን መቋቋም አለበት-ባዮች ናቸዉ።
------------------------------------------------------------------------------------
የተቃዉሞ ሠልፍ በበርሊን
እዚሕ ጀርመን የሚኖሩ ኢትዮጵያዉያን ደግሞ የአዲስ አበባ እና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ቆሟል መባሉን በጥርጣሬ ነዉ የተመለከቱት።ዛሬ በርሊን አደባባይ የተቃዉሞ ሠልፍ ያደረጉት ኢትዮጵያዉያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች እንደሚሉት የኢትዮጵያ መንግሥት ሠላማዊ ሠልፈኞችን በሐይል ደፍልቋል፤የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳን አሳልፎ ሰጥቷል በማለትም ወቅሰዋል።ጀርመንን ጨምሮ ምዕራባዉያን መንግሥታት በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና እንዲያሰርጉ ሠልፈኞቹ ጠይቀዋል።ይልማሐይለ ሚካኤል ሠልፉን ተከታትሎት ነበር።
ነጋሽ መሐመድ
ኂሩት መለሰ