1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የእድገት ጅምር በአፍሪካ

ሐሙስ፣ ጥር 19 1997

የተባበሩት መንግስታት ባቀረበዉ ዘገባ መሰረት ባለፈዉ አመት የምጣኔ ሃብት እድገት በአፍሪካ አገራትና በላቲን አገራት መታየቱን ገልጿል። ምንም እንኳን የነዳጅ ዘይት ዋጋ መለዋወጥ በአለም የምጣኔ ሃብት እድገታ ለዉጥ ላይ ጫና ቢያደርግም በአህጉሪቱ ካለዉ ዉስብስብ ችግር ባሻገር መጠኛ ለዉጥ በተወሰኑ አገራት ለመታየት መቻሉ የእሪካ የድገት ጅምር ሊባል ይቻላል።

https://p.dw.com/p/E0kW
ትናንት የወጣዉ የተባበሩት መንግስታት ያላፈዉ አመት የልማት እንቅስቃሴ ዘገባ እንደሚያሳየዉ በማደግ ላይ የሚገኙ አገራት በድጋሚ አሁንም የአለም የንግድና የምጣኔ ሃብቱ እድገት አንቀሳቃሽ ሞተር ሆነዋል።
ያም ሆኖ ግን በምዕተ አመቱ የልማት ግቦች ድህነትን በመቀነስ ረገድ ስድስት የአፍሪካ አገራት ብቻ ናቸዉ እንደታሰበዉ ሰባት በመቶ የሚሆነዉን አስፈላጊ የልማት እድገት ያሳዩት።
ዘገባዉ ይህ ለዉጥ ታይቶባቸዋል ያላቸዉ አገራትም አንጎላ፤ ቻድ፤ ኢኳቶሪያል ጊኒ፤ ኢትዮጵያ፤ ላይቤሪያና ሞዛምቢክ ናቸዉ።
የመንግስታቱ ድርጅት በተለይ የአሁኑ የአለም የምጣኔ ሃብትና የወደፊት ሁኔታ በሚለዉ ዘገባዉ እንደገለፀዉ ከሞዛምቢክ በስተቀር በሌሎቹ አገራት የታየዉ እድገት ከዘይት ኢንዱስትሪዉ ጋር በተገናኘ መልኩ ነዉ።
በልማት ረገድ የዘይቱ ዘርፍ ከፍተኛ የገንዘብ አቅም የሚፈልግ ሆኖ ድህነትን በመቀነስ በኩል በቀጥታ ለትዉልዱ የስራ ዕድል በመፍጠር አስተዋፅኦ ያደርጋል ይላል ዘገባዉ።
ያም ሆኖ ግን ከሌሎች የምጣኔ ሃብት ዘርፎች ጋር ካለዉ ያለፈና የወደፊት ግንኙነት ዉስንነት በመነሳት ሊኖር የሚገባዉ እድገት ትርጉም ባለዉ መልኩ ድህነትን ለመቀነስ አስችሏል ማለት አይቻልም።
በሶስት አገራት ማለትም በኮትዴቩዋር፤ በሲሼልስና ዚምባቡዌ በፓለቲካ አለመረጋጋት፤ አልፎ አልፎ በተከሰተዉ ድርቅና በሌሎች ተደራራቢ ጉዳዮች ሳቢያ የሚጠበቀዉ እድገት ባለፈዉ አመት አልታየም።
ዘገባዉ በቀረበበት ወቅት የመክፈቻ ስነስርአት ላይ የተባበሩት መንግስታት ምክትል ዋና ፀሃፊ ጆስ አንቶኒዮ ኦካምፖ ባለፈዉ አመት ከነበረበት ደረጃ በመነሳት የአለም ንግድና እድገት መሻሻል ጀምሯል ብለዋል።
ታይላንድና ሲሪላንካ ካላቸዉ ገቢ በቱሪዝሙ መስክ የሚያገኙት ስድስት በመቶ የሚሆነዉን ሲሸፍን በምጣኔ ሃብቱ ረገድ የተሻለ ዉጤት ያስመዘግባሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ባለፈዉ አመት የአለም ንግድ እድገት በቻይናና በህንድ መሪነት ከሁለት አመት በፊት 6.2 በመቶ የነበረዉ ወደ 10.5 በመቶ እንድገት አሳይቷል ቢባልም በያዝነዉ የፈረንጆቹ አመት ስምንት በመቶ ዝቅ ይል ይሆናል የሚል ስጋት አለ።
በአለም ዙሪያ የምጣኔ ሃብቱ እድገት የታየዉ ለዉጥ በተናጠል ሰባት በመቶ እድገት ባስመዘገቡት የምስራቅ እስያና የጋራ ብልፅግናዉ ህብረት አባላት በሆኑት አገራት የሚመራ ነዉ።
በቀረበዉ ዘገባ መሰረት ከምስራቅ እስያ በተጨማሪ በማደግ ላይ ያሉት አገራት በሚገኙባቸዉ የአለም ክፍልም ባጠቃላይ 5.5 በመቶ እድገት ታይቷል።
በአፍሪካ ከታየዉ እድገት 4.5 በመቶ የሚሆነዉ ከእርሻ ዉጤት የተገኘ ሲሆን የፓለቲካ ሁኔታዉ በተሻለ መልኩ መረጋጋትና የእርዳታ ለጋሾች ድጋፍ በተጨማሪም ጠንካራ የግብይት መድረክ በጪዉ አመት ቢኖሩ የተሻለ ዉጤት ይመዘገባል የሚል ተስፋ አለ።
በአፍሪካ የሚያሰጋዉ ዋነኛዉ ችግር ለመተንበይ አዳጋች የሆነዉ አየሩ ሁኔታ ሲሆን ይህም ከነዳጅ ዘይትም ሆነ ሚዛናዊነት ከጎደለዉ የገበያ ሁኔታ የከፋ ችግር የሚያስከትል ሊሆን እንደሚችል ባለሙያዎች ይናገራሉ።
በላቲን አሜሪካ ከሁለት አመት በፊት በኪሳራ የታየዉ የእድገት መጠን ባለፈዉ አመት5.5በመቶ የተለወጠ ሲህን ያም የሆነበት ምክንያት ብራዚል ባስመዘገበችዉ ፈጣን እድገትና ቬኒዙዌላና አርጀንቲናም ባሳዩት ማንሰራራት ነዉ።
በተባበሩት መንግስታት የቀረቡት ዘገባዎች ሁሉ ትኩረት ከፍተኛ መለዋወጥና ችግር በሚታይበት በነዳጅ ዘይት ገበያዉ ዙሪያ ሲሆን በአለም ዙሪያ ነዉ።
ባለፉት አመታት የሚፈለገዉን ያህል ማቅረብ ባለመቻሉ የነዳጅ ዘይት ዋጋ ማሻቀብ አስከትሎት ከነበረዉ ችግር ባሻገር አሁንም በግንባር ቀደምነት ከቻይና፤ ከአሜሪካና ከህንድ ከፍተኛ የፍላጎት ጥያቄ ይታያል።
በተያዘዉ እቅድ መሰረትም የዋጋ ችግር ሳይከሰት ፍላጎቱን ለሟላት ለዘንድሮ በአማካኝ ለአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዘይት ወደ 38 ዶላር ዝቅ የሚልበትን መንገድም ለመቀየስ እቅድ አለ።
ከምዕተ አመቱ የልማት እድገት እቅድ በአለም የሚታየዉን ድህነትና ርሃብ 50በመቶ መቀነስ፤ በሁሉም ስፍራ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርትን ማዳረስ፤ የህፃናትን ሞትና ከወሊድ ጋር በተገናኘ የሚከሰት የእናቶች ሞትን መቀነስ፤ የኤች አይቪ፤ የወባና የሌሎች በሽታዎችን ስርጭት መግታት ግንባር ቀደሞቹ ናቸዉ።