1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የእርስ በርስ ግጭት ያጠቃት ዑጋንዳ

ሐሙስ፣ ሚያዝያ 6 1997

ሰሜናዊ ዑጋንዳ የዛሬ 19 አመት ገደማ ፕሬዝዳንት ሙሴቪኒ ከጫካ ዉጊያ ወጥተዉ ስልጣን ከያዙበት ወቅት ጀምሮ አልተረጋጋችም። ህፃናትን በጦርነት ከመማገድ አንስቶ የሴቶች መደፈርና መጠለፍ የየዕለት ዜና በሆነበት በሰሜኑ አካባቢ የሚንቀሳቀሰዉ ራሱን The Lord Resitance Army በማለት የሰየመዉ የሽምቅ ተዋጊ ቡድን ከአገሪቱ አልፎ ለአጎራባች አገራትም ራስምታት ሆኗል።

https://p.dw.com/p/E0k3

የጎሳ ክፍፍልና ከተየያዩ ጥቅማጥቅሞች ጋር የተጎዳኘ የእርስ በርስ ግጭት ዑጋንዳን ጨምሮ ሌሎቹም የምስራቅ አፍሪካ አካባቢ አገራት የሚታመሱበት ግንባር ቀደም ችግር ነዉ።
በአስርቱ ትዕዛዛተ ዖሪት አገሪቱን እመራለሁ በማለት የሽምቅ ዉጊያ የሚያካሂደዉ The Lord Resistance Army የተሰኘዉ አማፂ ቡድን ዑጋንዳ ተረጋግታ ከድህነቷ ለመላቀቂያ መላ እንዳትፈልግ እንቅፋት ሆኗል ይላሉ የአገሪቱ የፓለቲካ ምሁራን።
በአንድ ወገን ስለ ሥርዓተ ክርስትናና እምነት እየሰበከ በሌላ ጎኑ በጥንቆላ አሰራር መተብተቡ የሚነገርለት ይህ ቡድን መነሻዉ የጎሳ ፓለቲካ ነዉ የሚልም ትችት አለ።
ያም ሆነ ይህ ግን የአገሪቱን ሰሜናዊ ክፍል በስፋት ይዞ ለዑጋንዳም ሆነ በሰሜን በኩል ለሚያዋስኗት ጎረቤቶቿ የራስ ምታት ሆኗል።
በማካራሬ ዩኒቨርስቲ የፓለቲካ ሳይንስ ዘርፍ መምህር የሆኑት ፓዉል ኦማህ እንደሚሉት ሰሜን ዑጋንዳ ባጠቃላይ እንደተጨቆነ የሚሰማዉ አካባቢ ነዉ።
ከአሁኑ መንግስት በፊት በአገሪቱ የነበረዉ ስርዓት ከተወገደበት ጊዜ አንስቶ የሰሜኑ ክፍል በተለያዩ ምክንያቶች አስታኮ አመፅ ጀመረ።
የLord resitance Army መስራች የሆኑት ሰሜነኞቹ የአቾሊ ጎሳዎች ሌሎች በአካባቢዉ ያሉ ጎሳዎችንም በስራቸዉ ለማሰባሰብ ችለዋል።
የአማፅያኑ እንቅስቃሴ በላንጎ፤ በአርብቶ አደርነታቸዉ በሚታወቁት በካራሞጃ ጎሳዎችና በቴሶ የጎሳ አባላት ድጋፍ ይታገዛል።
የዛሬ 19 ዓመት ህዝቡን አፍኖ ይገዛ የነበዉን የኮማንደር ቲቶ ኦኬሎ ሉዋታን አስተዳደር በማስወገድ ዩዌሪ ሙሴቪኒ ስልጣን ከያዙበት ጊዜ ጀምሮ ከሰላምና ዴሞክራሲ ይልቅ በዑጋንዳ አለመረጋጋት ተከስቶ ሰሜኑና ደቡቡ ወገን መከፋፈል ታየበት ባይናቸዉ ምሁራኑ።
የአገሪቱ ታሪክ ሲታይ ግን ዑጋንዳ ለረጅም ጊዜያት በተከታታይ ስትመራ የኖረችዉ ከሰሜኑ ክፍል በተገኙ አምባገነንና ጨካኝ መሪዎች ነበር።
ከእንግሊዞች ቅኝ አገዛዝ ከተላቀቀችበት ጊዜ አንስቶ ኢዲ አሚን፤ ሚልቶን ኦቦቴ፤ ባሲሎ ኦኬሎና ቲቶ ኦኬሎ ሉዋታ የተባሉት ወንማማቾች ሁሉ ስልጣን ላይ የወጡት ከሰሜኑ አካባቢ ካሉ ጎሳዎች ነዉ።
በዚያ ላይ የሰሜኑ ወገን ነዉ ከቅኝ ግዛት ዘመናቸዉ ጀምሮ በአገሪቱ የሚገኘዉን የታጠቀ የሰራዊት ኃይል የተቆጣጠረዉ።
ከዚያም ሰሜናዊ ያልሆኑት ሙሴቪኒ ስልጣን ሲይዙ አቾሊዎች የጅምላ ጭፍጨፋና የተድዶ መደፈር ሰለባ ሆነናል የሚል ክስ ጀመሩ።
በዚያ ላይ የቀድሞዉን ሰሜናዊ አገዛዝ ትደግፋላችሁ በመባል የሰብል ክምችታቸዉና ከብቶቻቸዉ ለአደጋ እንደተጋለጡ በዚያም ላይ ከጦር ሰራዊትነት እንደተባረሩ መግለፅ ቀጠሉ።
ሙሴቪኒ 60 በመቶ የሚሆነዉ ኃይል ከአቾሊ ጎሳ ብቻ የተሰባሰበበትን የጦር የጦር ኃይል በመለወጥ አገሪቱን በሚወክል ጦር በርዘዉ እንደገና ማቋቋማቸዉን የሚደግፉ በርካቶች ናቸዉ።
አቾሊዎች በጦር ኃይሉ ዉስጥ ለየት ያለ ሚና እንዳላቸዉ አድርገዉ ይቆትሩ ስለነበርና አንዳንዶቹም በከፍተኛ ስልጣን ላይ እንደነበሩ ይነገራል።
ለዚህም ይመስላል በሙሴቪኒ ተግባር ተበሳጭተዉ ከጦሩ በመዉጣት ከLord Resistance Army መሪ ከጆሴፍ ኮኒ ጋር የተቀላቀሉት።
ሙሴቪኒ ስልጣን ከያዙ በኋላ በሰሜኑ አካባቢ ከፈፀሟቸዉ ቅጣቶች መካከል አንዳንዶቹ የተፈፀሙት በከፍተኛ ባለስልጣናቶቻቸዉ ነዉ ይላሉ ምሁራን።
በወሳኝ የስልጣን እርከኖች ላይ ያስቀመጧቸዉ ባለስልጣናት የተመደበላቸዉን በጀት በሌላ አካባቢ ብቻ በማዋል ሰሜኑን ክፍል እየጎዱት ነዉ።
ምሁራኑ እንደሚያብራሩት በሰሜን ዑጋንዳ ያለዉ ጦርነት 20 አመት በመሙላቱና ባለስልጣናቶቹ ለአካባቢዉ አስፈላጊዉን ትኩረት በመንፈጋቸዉ የዚያ ወገን ህዝቦች ከማዕከላዊ መንግስት ፍፁም የራቁ እንደሆኑ ይሰማቸዋል።
ከተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት የተገኘዉ መረጃ እንደሚያመለክተዉ በሰሜን ዑጋንዳ ወደ1.4 ሚሊዮን የሚደርሱ ህዝቦች አብዛኛዎቹ የአቾሊ ጎሳ አባላት የሚገኙት በተበታተነ የመጠለያ ሁኔታ ነዉ።
የአገሪቱ ህገ መንግስት አንድ መሪ ለሁለት ዓመት ብቻ እንደሚያገለግል በሚያዘዉ መሰረት ምናልባት በሚቀጥለዉ ዓመት ሙሴቪኒ ከስልጣን ቢወርዱ የLord Resistance Army መሳሪያዉን ያስቀምጥ ይሆናል ተብሎ ይታሰባል።
ምሁራኑ እንደሚሉት ሙሴቪኒን የሚተካዉ ሰዉ ከየትናዉም አካባቢ መምጣቱ ችግር አይፈጥርም ዋናዉ ነገር ግን ተጨባጭ የሆኑ መመሪያዎችን መከተል ይኖርበታል።
በእነሱ እምነት አሁን ካለችበት አስከፊ የግጭት ሁኔታ ለመዉጣት ዑጋንዳ ብሄራዊ ህብረት ያስፈልጋታል።
በዚህ ረገድ የሚጠበቅ ተስፋ አለ። ምንም እንኳን የሚያስፈልገዉ የለዉጥ ሁኔታ በህገ መንግስቱ ገና ባይካተትም ህጋዊ በሆነ መልኩ የአገሪቱ መንግስት እያንዳንዱ ዞን የራሱ ክልላዊ መንግስት እንዲያቋቁም ተስማምቷል።