1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የእሢያ-ፓሢፊክ አ.ፔ.ክ. የኤኮኖሚ ትብብር

ረቡዕ፣ ኅዳር 13 1999

ባለፈው ሰንበት ቪየትናም-ሃኖይ ላይ የተካሄደው የእሢያ-ፓሢፊክ የኤኮኖሚ ትብብር መድረክ የመንግሥታት መሪዎች ጉባዔ የዓለም ንግድ ድርድርን ለማነቃቃት በመስማማት ተከናውኗል። አስተናጋጇ አገር በአዘጋጅነት ብቃቷ አድናቆትን ስታተርፍ ጉባዔው በአጠቃላይ ስኬታማ ሆኖ ነው የታየው።

https://p.dw.com/p/E0dK
ምስል AP

የሃኖዩ መድረክ የአሜሪካ፣ የጃፓን፣ የቻይና፣ የደቡብ ኮሪያና የሌሎች አገሮች ኩባንያዎች ከቴክኖሎጂ እስከ ፊናንስ፤ ከማዕድን እስከ አገልግሎት ሰጪው ዘርፍ በተለያዩ መስኮች በርካታ ውሎች የተፈራረሙበት ነበር። 21 የመንግሥታት መሪዎች በተሳተፉበት ጉባዔ አሥር ሺህ የሚሆኑ ባለሥልጣናት፣ የንግድ ዘርፍ ተጠሪዎችና ጋዜጠኞች የሃኖይን ገጽታ ለሁለት ቀናት አድምቀው ሰንብተዋል። የመንግሥታቱ ጉባዔ የተካሄደበት ኮንቬንሺን ሤንተር የተሰኘ ማዕከል ግንቢያ ሁለት ዓመት ሲፈጅ የታነጸው በ 270 ሚሊዮን ዶላር ነበር።

ቪየትናም 750 ዶላር በሚሆን የሕዝብ ዓመታዊ ነፍስ-ወከፍ ገቢ ድሃ ተብላ የምትቆጠር አገር ብትሆንም የአስተናጋጅነት ብቃቷ ከፕሬዚደንት ቡሽ እስከ ቭላዲሚር ፑቲን ብዙዎች የመንግሥታት መሪዎችን ማስደነቁ አልቀረም። ቢሆንም ሰባት በመቶ በሆነ በተፋጠነ ዓመታዊ ዕድገት ላይ የምትገኘው አገር መሪዎች አስተያየት ለየት ለየት ያለ ነው። የአገሪቱ የንግድ ዘርፍ በዓለምአቀፍ ደረጃ ለተፎካካሪነት ለመብቃት የሚያደርገው ጥረት ቀላል ባይሆንም በስኬት አቅጣጫ ነው የሚያመራው። ቪየትናም ከሁለት ሣምንታት በፊት የዓለም ንግድ ድርጅት ዓባል ሆና ተቀባይነት ማግኘቷም ያለ ምክንያት አይደለም።

የአገሪቱ መንግሥት ከአኤኮኖሚው እንቅስቃሴ ባሻገር ሙስናን በመታገሉ ረገድም ታላቅ ዕርምጃ አሣይቷል። በቪየትናም ሰፊ ተቀባይነት ማግኘት ወደ አገሪቱ የሚገባው የውጭ ቀጥተኛ ካፒታል በዚህ ዓመት ከ 8 ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደሚዘልቅ ነው የሚጠበቀው። በአጠቃላይ በፓሢፊክ ውቂያኖስ አኳያ የሚገኙት አገሮች ስብስብ በዓለም ንግድ ላይ ታላቅ ድርሻ ያለው ነው። እነዚህ አገሮች ግማሽ ገደማ የሚጠጋውን የዓለም ንግድ ድርሻ የሚይዙ ሲሆን በዓለምአቀፍ ደረጃ 70 በመቶው የኤኮኖሚ ዕድገት ጎልቶ የሚታየውም በዚሁ አካባቢ ነው። የአሜሪካው ፕሬዚብርቱ ጉዳትን የሚያስከትል ነው።

የዶሃው የዓለም ንግድ ድርድር ዙር ተሰናክሎ እስከቀጠለና መልሶ መንቀሳቀስ እስካልቻለ ድረስ የበለጸጉት መንግሥታት መድሕናቸውን የአካባቢና የሁለት ወገን ነጻ የንግድ ውል በማስፈን እንደሚሹ አንድና ሁለት የለውም። በዚህ ተጎጂዎቹ ደግሞ ታዳጊዎቹ አገሮች ናቸው። ገና ከአሁኑ ከሁለት መቶ የሚበልጡ፤ በሁለት መንግሥታት ወይም የአገሮች ስብስብ መካከል ገበያ የሚከፍቱና ቀረጥን የሚቀንሱ ይህን መሰል የንግድ ውሎች ሰፍነው ይገኛሉ። ተጨማሪ 90 ውሎች በፊርማ ጸድቀዋል ወይም እየተጠናቀቁ ነው። ከአሥር ዓመታት በፊት ከነበረው ሲነጻጸር አሃዙ በእጥፍ አድጎ ይገኛል። መለስ ብሎ ለማስታወስ ያህል በ 1990 ዓ.ም. በዓለም ንግድ ድርጅት ቀደምት፤ በአጠቃላዩ የቀረጥና የንግድ ውል ማሕበር በ”ጋት” ዘመን በሁለት መንግሥታት ወይም በአካባቢ ደረጃ የተፈረሙት ውሎች ከ 31 አይበልጡም ነበር። ሃያ ዓመታት ቀደም ሲል እንዲያውም ስድሥት ብቻ ነበሩ።

በዓለም ዙሪያ ከተናጠል አገሮች ወይም አካባቢዎች ጋር የነጻ ንግድ ውል በማስፈኑ በኩል በተለይ ቀደምት ሆና የምትገኘው አሜሪካ ናት። በዚህም አሜሪካ አማራጭ መንገድ ማግኘቷ ብቻ ሣይሆን የዓለም ንግድ ድርጅትን የምትጫንበት መሣሪያ እያገኘች ነው። በዓለም ንግድ ድርጅት ውስጥ ፍላጎቷን ማራመድ እስከቻለች ድረስ በዚያው ትገፋበታለች። ካልሆነ ግን አሁን እምደሚታየው ወደ ሁለት ወገኑ ውል ነው የምታሽገሽገው። ዋሺንግተን ለምሳሌ ባለፉት ዓመታት በላቲን አሜሪካ ከ 11 አገሮችጋር የሁለት ወገን የንግድ ውል ወይም ባይላተራል ስምምነቶች አድርጋለች። የአውሮፓ ሕብረት በአንጻሩ በአካባቢው ይህን መሰሉን ውል ለማስፈን የቻለው ከሜክሢኮና ከቺሌ ጋር ብቻ ነው።

የበለጸጉት መንግሥታት ከሁሉም በላይ ደግሞ በተፋጠነ የኤኮኖሚ ዕድገት ላይ ከሚገኙት የእሢያ አገሮች ጋር በሚያደርጉት የምርት ልውውጥ የንግድ ማቃለያ ሁኔታን ለማስፈን አጥብቀው መጣራቸው አልቀረም። የአሜሪካው ፕሬዚደንት ጆርጅ ቡሽ በሃኖዩ የእሢያ-ፓሢፊክ ጉባዔም የአካባቢው የነጻ ንግድ ክልል እንዲፈጠር የሚያደርጉትን ግፊት ቀጥለውበት ታይተዋል። የአውሮፓ ሕብረትም እንዲሁ ከሕንድና ከአዜያን ማሕበር ዓባል መንግሥታት ጋር ይህንኑ ውል ለማስፈን ጥያቄውን አቅርቧል። የወቅቱ አዝማሚያ ይህ ሲሆን በሌላ በኩል ግን በዓለም ንግድ ድርጅት ጥላ ሥር የሚደረግ ስምምነት ይበልጥ ይበጃል የሚል አስተያየት ከያቅጣጫው መሰንዘሩም አልቀረም።

የጀርመን የውጭ ንግድ ማሕበር ፕሬዚደንት አንቶን በርነር ለምሳሌ በዓለም ንግድ ድርጅት ውስጥ የሚደረግ ስምምነት ለመላው 149 ዓባል ሃገራት የሚበጅ በመሆኑ የበለጠ ጠቀሜታ አለው ባይ ናቸው። ግን የዓለም ንግድ ድርጅት በዚህ መሥመር መንቀሳቀስ ካልቻለ እርሳቸውም ቢሆን ለሁለት ወገኑ ውል አማራጭ አይታያችውም።
ከሆነ በተለይ የረባ የጥሬ ሃብት የሌላቸው ትናንሽ አገሮች ከበለጸጉት መንግሥታት ጋር በሚኖራቸው የንግድ ግንኙነት ተገቢውን ክብደት አያገኙም ማለት ነው። በርነር እንደሚሉት ጥቅማቸውን የሚያስጠብቅ የሁለት ወገን ውል ማስፈኑ ከናካቴው ከባድ ነው የሚሆንባቸው።
እነዚህ አገሮች ባለባቸው የሰው ሃይል እጥረትና ዝቅተኛ አቅም የተነሣ በኤኮኖሚ ታላላቅ ከሆኑት አገሮች፤ ከጃፓንም ሆነ ከአሜሪካ ወይም ከአውሮፓ ሕብረት ጋር ጥቅማቸውን የሚያስከብር ውል ለማስፈን አይችሉም። ምርጫቸው በረጅም ጊዜ የተሻለ ተሥፋ ወደሚሰጧቸው ወደ ቻይና ወይም ሕንድ ማዘንበል ነው የሚሆነው።
በእርግጥም የወቅቱ አዝማሚያ ይህን የሚመስል ነው። በአፍሪቃም ሆነ በእሢያ ብዙዎች ታዳጊ አገሮች የረጅም ጊዜ የልማት ዕጣችውን ከቻይና ጋር ማስተሳሰር ይዘዋል። በቅርቡ ቤይጂንግ ላይ ተካሂዶ የነበረው የቻይናና የአፍሪቃ መንግሥታት መሪዎች ጉባዔ፤ በአጠቃላይም ቻይና እያስፋፋች ያለችው የወዳጅነት ትብብር በቂ ምሳሌ ነው።