የኤርትራ ፖለቲካዊ ሁኔታ
ረቡዕ፣ ጥር 22 2005
በቅርቡ የኤርትራ የማስታወቂያ ሚንስቴር ለጥቂት ሰዓታት ይዘው የነበሩ ወታደሮች ሚኒስቴሩን ከለቀቁ በኋላ የኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናቱን ከስልጣን ማሰናበቱ ተነግሯል ። የኤርትራ መንግስት ተወሰደ ስለተባለው እርምጃ ከኤርትራ መንግሥት በኩል የተሰማ ነገር የለም ። ሆኖም እንደተባለው የባለስልጣናቱ መባረር እውነት ከሆነ የኤርትራን ፖሊቲካ ቀውስ እንደሚያባብስ ይነገራል። ገመቹ በቀለ በጉዳዩ ላይ አንድ የቻተም ሃውስ የፖሊቲካ ተንታኝ አነጋግሪሮ ተከታዩን ዘገባ አጠናቅሯል ።
ከጥቂት ቀናት በፊት ወደ መቶ የሚጠጉ የኤርትራ መንግስት ወታደሮች አመጽ ከከሸፈ በኋላ የኤርትራ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናቱን ከቦታቸው ማንሳቱን በተቃዋሚዎች ድህረ ገጾች የወጡ መረጃዎች አመልክተዋል። አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ በአስመራ የሚኖሩ ኤርትራውያን ጠቅሶ እንደዘገበው ከአመጹ በኋላ በርካታ ሰዎች ታስረዋል። የኤርትራ መንግስት ግን ለክሱ የአጸፋ መልስ አልሰጠም። የባለስልጣናቱ ከኃላፊነታቸው መነሳት በኤርትራ የሚታየውን የፖሊቲካ ችግር ያባብሳል ባይ ናቸው በቻተም ሃውስ የአፍሪቃ ቀንድ የፖሊቲካ አዋቂው አህመድ ሱሌይማን፤
«የኢሳያስ መንግስት ባለፉት ጊዜያት በዙሪያው የሚገኙ ሰዎችን ብቻ ይዞ ይንቀሳቀስ ነበር። ለህገ መንግስቱና ፖሊቲካ ነጻነት በተካሄዱ የመንግስት ግልበጣ ሙከራዎች እና በተቃዋሚዎች ምክንያት የኢሳያስ መንግስት የፖሊቲካ መዳውን ይበልጡን አጥቧል። አሁንም ደግሞ ይፈጠራል ብለን የምንገምተው ይህ ነው።»
ለባለስልጣናቱ ከስልጣን መነሳት ምክንያት የሆነው ጥር 13 የተካሄደው የኤርትራ ወታደሮች አመጽ መሆኑ ይነገራል። አመጹ በአንድ በኩል የኢሳያስ መንግስት ለስልጣኑ የሚያሰጋውን ሰዎች ለማስወገድ ሆን ብሎ ያቀነባበረ የፈጠራ ሴራ ነው የሚሉ ሲኖሩ፣ በሌላም በኩል በኤርትራ መንግስት ወታደሮች መጥፎ አያያዝና ዝቅተኛ ደመዎዝ ምክንያት ቀድሞውኑ ይጠበቅ ነበር ይላሉ። ሆኖም ዘገባዎች በቀላሉ ከማይገኙበት አስመራ ትክክለኛውን ምላሽ ማግኘት ይከብዳል ባይ ናቸው አህመድ ሱሌይማን፤
«የኤርትራ መንግስት ታሪክና በሀገሪቷ ያሉ እንቅስቃሴዎችን የመቆጣጠር ችሎታው ይህ አሉባልታ እንዲሰራጭ ሰበብ ሊሆን ይችላል። ሆኖም ምናልባት መንግስት የበላይነቱን ለማሳየት የሚቃወሙትን ያሰቃያል፤ ወይም ደግሞ በኤርትራ ማስታወቂያ ሚኒስቴር የታየው ትክክለኛ አመጽ ሊሆን ይችላል ብሎ ጣት ቀስሮ መናገር ይከብዳል።»
አንዳንድ ዘገባዎች እንደሚያመልክቱት በኢሳያስ አፈውርቂና በከፍተኛ የጦር መኮንኖቻቸው መካከል ከፍተኛ ቅራኔ እንዳለ ይነገራል። ፕሬዚዳንቱ የጦር ሚኒስትራቸውን ሳያሳውቅ የህዝብ ሚሊሻዎች የጦር መሳሪያ እንዲታጠቁ ማዘዛቸው ተገልጿል። ከሳምንት በፊት ወታደሮቹ ያመጹት ምናልባት ይህ ቅራኔ ከገደብ ስላለፈ ይሆናል የሚሉ ወገኖች አልታጡም። የቻተም ሃውሱ አህመድ ሱሌይማንም የነኚህ ወገኖች መላምት ትክክል ሊሆን ይችላል ይላሉ፤
«በኤርትራ ውስጥ ዜጎችን ማስታጠቅ አዲስ አይደለም። ብዙ ሰዎች እንዲታቁ ይገደዳሉ። ከጦር ኃይሉ ውጭ ለኢሳያስ ታማኝ የሆኑ ሚሊሻዎችን ማስታጠቅ በትክክል ሊሆን የሚችል ጉዳይ ነው።»
ገመቹ በቀለ
ሒሩት መለሠ