1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኤርትራ ስደተኞች

ረቡዕ፣ ኅዳር 1 2008

በሜዲትራንያን በኩል አድርገው ወደ አውሮፓ በጀልባ ከሚሰደዱ አፍሪቃውያን መካከል አብዛኞቹ ኤርትራውያን እንደሆኑ ይነገራል። በግምት ወደ አንድ ሚልዮን የሚጠጉ ኤርትራውያን፣ ወይም ከሕዝቧ መካከል አንድ አምስተኛው በውጭ ሀገር ይኖራል። ሀገሪቱ በአምባገነን አገዛዝ ስር ያለች «የአፍሪቃ ሰሜን ኮርያ» ነችም ይሏታል።

https://p.dw.com/p/1H46q
Griechenland Flüchtlinge aus Eritrea vor Rhodos
ምስል picture alliance/AP Photo

[No title]

«እያንዳንዱ ዜጋ ለውትድርና የሚገደድበት እና ህዝብ የሚጨቆንባት ሀገር» እንደሆነችም ይነገራል። የሚሰደድ ማንኛውም ዜጋ እንደ ከሀዲ ነው የሚታየው። እንደዛም ቢሆን ግን ሀገሪቱ ውጭ የተሰደዱ ዜጎቿ በሚልኩት የውጭ ምንዛሪ ላይ ጥገኛ ናት። ስምረት አርአያ ምስራቅ ኤርትራ ውስጥ የበቆሎ እርሻዋን ትኮተኩታለች። የበቆሎ ችግኞቿ ውሀ የሚያገኙት በየ 30 ሴንቲ ሜትሩ ርቀት ቀዳዳ ባለው ወፍራም ጎማ ነው።
ውሃው ከአንድ ሰው ሰራሽ ሀይቅ የሚገኝ ሲሆን፣ ወደማሳዎቹ የሚደርሰው በኤሌክትሪክ በሚሰራ የውኃ ቧምቧ አማካኝነት ነው። ይህ ግን የሚሰራው የኤሌክትሪክ ኃይል ያለ ቀን ነው። ምክንያቱም ብዙውን ጊዜ ኮረንቲ ይቋረጣል። የስምረት አርአያ ችግር ግን ይህ ብቻ አይደለም።« ጥቅም እንኳን የለውም። ብዙ ክፍያ አለው። ለምሳሌ ለግብር 325፣ ለሰራተኛ፣ በየወሩ ደግሞ ለጥበቃ 25 እንከፍላለን ። ከዚያ በላይ ለውኃ፣ የውኃውን መስመር ለሚከፍቱት እንከፍላለን። ጥቅሙ ትንሽ ነው።ብዙ ወጪ ነው ያለው።»
ኤርትራ ከዓለም ደሀ ከሚባሉት ሀገራት ተርታ ትሰለፋለች። ለዚህም ነው በየዓመቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ኤርትራውያን አደገኛውን የባህር ጉዞ ለመጓዝ የሚደፍሩት። ይሁንና፣ ባለፈው ሰኔ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ባወጣው ዘገባ መሰረት፣ ይህ ዋነኛው የስደት ምክንያት አይደለም። የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ኃላፊ ሼኢላ ኬትሩት።« ኮሚሽኑ እንደደረሰበት ከሆነ ኤርትራ ውስጥ ሆን ተብሎ ግዙፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተፈጽሞዋል፣ ዛሬም እየተፈጸመ ነው። ይህም የሚደረገው በመንግሥት ትዕዛዝ መሠረት ነው ።»
የኮሚሽኑን ወቀሳ አስመራ የሚገኘው መንግሥት በተደጋጋሚ አወግዟል። በናይሮቢ የሚገኙት የኤርትራ አምባሳደር አቶ በየነ ርዕሶምም ወቀሳው መሠረተ ቢስ እንደሆነ ነው የሚናገሩት።« ደንግጬአለሁ፣ ማመን ያልቻልኩት እና ግራ ያጋባኝ ነገር ነው። ምክንያቱም ይህ ዘገባ እጅግ የሚያስጠላ እና አሳፋሪ ነው። ይህ በማህበረሰባችን፣ በመንግስታችን ፣ በህዝባችን እና በወዳጆቻን ላይ የተቃጣ ትክክለኛ ያልሆነ ጥቃት ነው።»
ለምሳሌ የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት አምነሲቲ ኢንተርናሽናል ከ 10 000 በላይ የፖለቲካ እስረኞች በአሰቃቂ ሁኔታ በእስር ላይ እንደሚገኙ ፤ ሰዎች እንደሚገረፉ እና እንደሚገደሉ በመጥቀስ ያወጣውን ዘገባ የኤርትራ መንግሥት «ተረት» ሲል አጣጥሎታል፤ በስደት ላይ የሚገኙት ኤርትራዊው ሀኪም አብረሃም ግን የአይን እማኝ በመሆን ስለዚሁ የአምነስቲ ወቀሳ በግልጽ ይናገራሉ።« የቆሰሉ በተለይ እጃቸው ላይ የቆሰሉ ሰዎችን አክሜያለሁ። ይህም እጃቸውን ታስሮ ስለቆየ የመጣ ነው።እና ከቁም ስቅል የመጣ ነው። »
ሀገር ውስጥ የሚገኙ ኤርትራውያን ግን በጣም ስለሚፈሩ በግልጽ እንዲህ ለመናገር አይደፍሩም ትላለች ዘጋቢዋ ሊንዳ ሽታውደ። የነፃነቱ ትግል ከበቃ ከ20 ዓመታት በኋላ ኤርትራ አሁንም ዜጎቿን ለውትድርና የምታሰልፈው ከኢትዮጵያ ጋር ባለው ውዝግብ የተነሳ እንደሆነ ነው የኤርትራ ፕሬዚደንት አማካሪ አቶ የማነ ገብረአብ የሚያስረዱት።« ችግሮች ነበሩ። በጦርነቱ ምክንያት የተነሳ 18 ወራት የሚቆይ ብሔራዊ ውትድርና አለን። አንዳንድ ወጣቶቻችን በውትድርና ለረዥም ጊዜ እንዲቆዩ ተገደዋል። »
ከዚሁ ብሔራዊ ውትድርና አገልግሎት ለማምለጥ እያሉም በርካታ ኤርትራውያን ሀገር ጥለው ላይመለሱ ይሸሻሉ። የሚያስገርመው ግን፣ ኤርትራ ከእነዚህ በውጪ የሚኖሩ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎችዋ ጥገኛ መሆኗ ነው። የሚልኩት ገንዘብ በግምት ከሀገሪቷ ጠቅላላ ገቢ አንድ ሶስተኛውን እንደሚሸፍን ነው የሚነገረው።
ሊንዳ ሽታውደ/ ልደት አበበ
አርያም ተክሌ

Menschenrechtsaktivistin Meron Estefanos
የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ሜሮን እስጢፋኖስምስል DW/Meron Estefanos
Schweden Ankunft Flüchtlinge aus Eritrea
የኤርትራ ስደተኞች ስዊዲን ሲገቡምስል picture-alliance/dpa/R. Nyholm