የኢትዮጵያ ግዙፍ ግድብና የግብፅ ተቃዉሞ
ረቡዕ፣ መጋቢት 3 2006ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ የምታስገነባዉ ግዙፍ የኤሌክትሪክ ሐይል ማመንጫ ግድብ ግንባታ የተጀመረበትን ሰወስተኛ ዓመት ለማክበር እይተዘጋጀች ነዉ።ግድቡ ወደ ግዛቷ የሚፈሰዉን የዉኃ መጠን ይቀንሰዋል የሚል ሥጋት ያደረባት ግብፅ ባንፃሩ ሥለ አባይ የዉኃ አጠቃቀም አዲስ ዉል እንዲደረግ አዲስ ዲፕሎማሲያዉ ዘመቻ ጀምራለች።አንዳድ ዘገቦች እንደጠቆሙት የግብፅ ባለሥልጣናት የፋርስ ባሕረ-ሠላጤ አካባቢ ሐገራት በተለይም ስዑዲ አረቢያ ለሽምግልና ጣልቃ እንድትገባ ጠይቀዋል።በኢትዮጵያ ላይ ተፅዕኖ እንዲደረግም ግብፅ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ መጀመሯ ሲዘገብ ኢትዮጵያም ለአፃፋ ዲፕሎማሲ መዘጋጀትዋ እተነገረ ነዉ።ወዴት ያመራ ይሆን? ነጋሽ መሐመድ አጭር ዘገባ አለዉ።
ወዴት ያመራል? ዲፕሎማሲያዊዉ ፍትጊያ ምናልባትም የመገናኛ ዘዴዎቹ ፕሮፓጋንዳ፤ የቃላት እንኪያ ሠላንቲያዉ-ይቀጥላል-ይላሉ ISS በሚል ምሕፃረ-ቃል የሚጠራዉ የፀጥታ ጥናት ተቋም ሐላፊ ዶክተር ያኪ ሲልየ።
«ዉጥረቱ ሲባባስ ማየታችን አይቀርም ብዬ አስባለሁ።መረር-ጠንከር ያለ ዉዝግብ እናይም ይሆናል።»ለምን? የአባይን የዉኃ ፍሰት አጠቃቀም ለሚያዉቅ የሞኝ ጥያቄ ይመስላል።ግን አይደለም ግብፅ ወደ ግዛቷ የሚፈሰዉ የዉኃ መጠን እንዲቀንስ አትፈልግም።ኢትዮጵያ ባናፃሩ የጀመረችዉን ማቋረጥ የማይታሰብ ነዉ።እና ሲጀመር ጀምሮ-ዉዝግቡ ነበር።
«ገና ከጅምሩ አወዛጋቢ ነበር።የ1956ቱ ስምምነት አለ።ስምምነቱ አብዛኛዉን የአባይ ዉኃ ለግብፅና ለሡዳን የሚሰጥ ነዉ።አሁን ደግሞ ኢትዮጵያ የታላቁን የሕዳሴ ግድብ ዕቅድና ዓላማ ከደረቷ ሥር ሸሽጋ ሚስጥር አድርጋዋለች።ግንባታዉ በዉኃዉ ፍሰት የሚያደርሰዉን ተፅዕኖ በሚስጥር ይዛ ግንባታዉን ሥትጀምር ነገሮች በፍጥነት ተለዋወጡ።»
ዉዝግቡም ቀጠለ።የኢትዮጵያ፤የግብፅና የሱዳን የዉሐ ሚንስትሮች በቴክኒካዊ ጉዳዮች ላይ ያደርጉት የበረዉ ዉይይት ከከሸፈ ወዲሕ ደግሞ ዉዝግቡ-ወደ ዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ ተለወጠ።አንዳድ ዘገቦች እንደጠቆሙት ሳዑዲ አረቢያ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትሸምግላት ግብፅ ጠይቃለች።ሌሎች ሐገራትም በኢትዮጵያ ላይ ግፊት እንዲያደርጉ ካይሮዎች እየጠየቁ ነዉ።ዶክተር ሲሊየ እንደሚሉት ግን ኢትዮጵያ ለዉጪ ግፊት የምትንበረከከ አትመስልም።
«የግንባታዉ ወጪ በአብዛኛዉ ከቦንድ ሽያጭና ከሀገር ዉስጥ ገቢ የሚሸፈን ነዉ።ሥለዚሕ የዉጪ ግፊት የኢትዮጵያዉያኑን ዕቅድ የሚያስለዉጥ አይደለም።ከግድቡ ሥራ አንድ ሰወስትኛዉ ወደ መጠናቀቁ ነዉ። ኢትዮጵያዉያን ግንባታዉን ይቀጥላሉ።የግብፆችን ሥጋት ለማርገብ የሆነ ማካካሻ ያደርጉም ይሆናል።ግንባታዉ ግን ይቋረጣል ብዬ ጭራሽ አላስብም።»
የማካካሻዉ ምን-እንዴትነት ግብፆችን ማርካት አለማርካቱም አይታወቅም።የማይታወቀዉ ማካካሻ ባይኖር፤ ወይም ግብፆች ማካካሻ የሚባለዉን እንቢኝ ቢሉስ?አሁን የጦዘዉ ዉዝግብ ወዴት ያመራ ይሆን?- የሲልየ መልስ-ወዴትም አይነት-ነዉ።በሁለት ምክንያት።
«ሱዳን የግድቡን ግንባታ ሥትደግፍ የግብፆች አቅም በጅጉ ተዳክሟል።ሁለተኛ ምክንያት በግልፅ የምናየዉ ግብፅ ዉስጥ ያለዉ ብጥብጥ ነዉ።የግብፅ መንግሥት በሀገር ዉስጡ ችግር ተወጥሯል።ከጥቂት አመታት በፊት የአረብ ሕዝባዊ አብዮት ከመቀጣጠሉ በፊት ቢሆን ኖሮ ነገሩ ካሁኑ የበለጠ አሳሳቢ በሆነ ነበር።»
ካሁኑ የበለጠ ያሳስብ ነበር-ማለት ግን አሁን አያሳስብም ማለት አይደለም።ግድቡ ሲጠናቀቅ ስድስት ሺሕ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ያመነጫል።ከኃሐይሉ ግብፅም ተጠቃሚ ትሆናለች ነዉ-የሚባለዉ።ግን ግድቡ ለኢትዮጵያ እንደ ብሔራዊ ክብር የሚታይ ነዉ።ለግብፆች ባናጻሩ የአባይ ዉኃ መቀነስ ክብሔራዊ ፀጥታ-መናጋት የሚቆጠር ነዉ።
ነጋሽ መሐመድ
ተክሌ የኋላ