የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ክፍል ሁለት
ረቡዕ፣ የካቲት 5 2006
ከ4000 ዶላር በላይ ከሆነ ደግሞ መካከለኛ እና ከ 1000 ዶላር በታች ከሆነ ግን ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ደኃ ኣገሮች ተብለው ይመደባሉ። ኢትዮጵያም የምትሰለፈው በዚሁ መደዳ ሲሆን ባለፈው ሳምንት ዝግጅታችን ለመዳሰስ እንደተሞከረው ኢትዮጵያ ጎረቤት ኬኒያ ኣሁን ከምትገኝበት የእድገት ደረጃ ለመድረስ እንኩዋን የኢኮኖሚ እድገትዋ ከ 7 በመቶ ሳይወርድ ቢያንስ ለሚቀጥሉት አራት አስርተ ዓመታት ያህል ባለማቁዋረጥ ማደግ ይኖርባታል። ይህም የሚያመለክተው የድህነቱ ወለል ምን ያህል ጥልቀት እንዳለው ነው።
የዓለም ባንክም ሆነ ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቁዋም IMF ቢሆኑ ሙሉ በሙሉ ባይስማሙበትም የኢትዮጵያ መንግስት ካለፉት 10 ዓመታት ወዲህ 11 በመቶ የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገበ መሆኑን ሲገልጥ ቆይተል። ይህ በእርግጥ ለዘመናት ከድህነት ወለል በታች ለምትዳክረው ኢትዮጵያ የሚያበረታታ ዜና ሆኖ ሳለ የተባበሩትመንግስታት ድርጅት ከሁለት ሳምንታት በፊት ይፋ ባደረገው የ2014 ዓመታዊ ዘገባ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እድገት ባለሁለት ዓኃዝ መሆኑ ቀርቶ ባለኣንድ ዓኃዝ ሆኖ እንደሚቀጥል እና ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታትም ከ 6,4 በመቶ ሊበልጥ እንደማይችል ኣስታውቀዋል። ኣፍሪከን ኢኮኖሚክ ሪፖርት የተሰኘው ዘገባ እንዲያውም ወደ 6,3 ከመቶ ሲያወርደው ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቁዋም IMF እና የዓለም ባንክ ግን 7,5 ሊደርስ እንደሚችል ይተነብያሉ። የኢትዮጵያ ባለስልጣናት በበኩላቸው ኣሁንም ቢሆን የኣገሪቱ እድገት በነበረበት ይቀጥላል ሲሉ ይከራከራሉ።
ባለፈው ሳምንት ዝግጅታችን በUS አሜሪካ ቨርጂኒያ ክ\ኃገር በኮሌጅ ኦፍ ዊሊያም አንደ ሜሪ የኢኮኖሚክስ መምህር ከሆኑት ፕሮፌሰር ብርኃኑ አበጋዝ ጋር ባደረግነው ውይይት የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ቀንሰዋል ሲባል ከምን የተነሳ እንደሆነ እንዲያስረዱን ጠይቀናቸው ነበር ለዛሬ በይደር ያቆየነው። ዛሬም ለዚሁ ጥያቄ ምላሽ በመስጠት ይጀምራሉ ፕሮፌሰር ብርኃኑ አበጋዝ። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ማነቆዋችስ ምንድናቸው የሚለው የበርካቶች ጥያቄ ሲሆን ፕሮፌሰር ብርኃኑ አበጋዝ ምላሽ ኣላቸው።
የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ እድገት ኣስመልክቶ የተለያዩ ወገኖች የየራሳቸውን ግምገማና ግምት ቢሰጡም የኢትዮጵያ መንግስት ግን ኣሁንም ቢሆን እድገቱ ባለ ሁለት ዓኃዝ ሆኖ እንደሚቀጥል ነው እየገለጠ ያለው። አቶ ኃጂ ኢብሳ የገንዘንና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር ባለሙያ፤
ጠ\ሚ ኃ\ማሪያም ደሳለኝ ባለፈው ሰኞ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ዘንድሮም ባለሁለት ዓኃዝ ሆኖ በነበረበት እንደሚቀጥል ነው የተናገሩት። ከዓለም ዓቀፉ ተቁዋማት ጋር የተመድን ጨምሮ የዓለም ባንክ እና ዓለም ዓቀፉ የገንዘብ ተቁዋምን ማለታቸው ነው በትንበያ ደረጃ ተስማምተን ኣናውቅም ያሉት ጠ\ሚ ኃ\ማሪያም ደሳለኝ የኃላ ኃላ ግን መቀራረባችን የተለመደ ነው ብለዋል።
ጃፈር ዓሊ
አርያም ተክሌ