1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ስብሰባ በብራስልስ

ዓርብ፣ ነሐሴ 27 2008

የአፍሪቃ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ በኢትዮጵያ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ የሚመለከታቸው ወገኖች ልዩነታቸውን በድርድር እንዲፈቱ ጥሪ አቅርበዋል።

https://p.dw.com/p/1Jv4i
Äthiopien Protest
ምስል Reuters/T. Negeri

[No title]

በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ትናንት በብራስልስ፣ ቤልጅየም ስብሰባ ተካሄዷል። ስብሰባውን የጠሩት እና በጋራ ያዘጋጁት የአፋር ሰብዓዊ መብት ድርጅት እና የአውሮጳ ምክር ቤት አባል የሆኑት የእንደራሴ አና ጎሜሽ ቢሮ ናቸው።
የአፍሪቃ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ በኢትዮጵያ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ የሚመለከታቸው ወገኖች ልዩነታቸውን በድርድር እንዲፈቱ ጥሪ አቅርበዋል። በኅብረቱ ድረ-ገፅ በሰፈረው መልዕክታቸው ዶ/ር ንኮሳዛና ድላሚኒ ዙማ ባለፉት ጥቂት ወራት በኢትዮጵያ የተቀሰቀሰው እንደሚሳስባቸው ገልጠዋል። ሊቀ-መንበሯ ሁሉም ወገኖች እንዲታቀቡም ጥሪ አስተላልፈዋል።
በኢትዮጵያ በተቀሰቀሰው ተቃውሞ ከመንግስት ጋር ግንኙነት ያላቸው የአበባ እርሻዎች መቃጠላቸውን አንድ የሆላንድ ኩባንያ አስታውቋል። ኢትዮጵያ ለውጭ ገበያ የምታቀርበው የአበባ ምርት አገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ከምታገኝባቸው ዘርፎች አንዱ ነው። ኤስሜራልዳ የተሰኘው ኩባንያ በባህር ዳር ከተማ አስር ሚሊዮን ዩሮ ወጪ የተደረገበት የአበባ እርሻ በተቃዋሚዎች በእሳት መጋየቱን እና ሌሎች የአበባ እርሻዎችም በቀጠለው ተቃውሞ መጎዳታቸውን ገልጧል።
የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ካውንስል መንግስት በተቃዋሚዎች ላይ ያልተመጣጠነ ኃይል መጠቀሙን ገልጧል። የምዕራባውያን የቅርብ አጋር የሆነው የኢትዮጵያ መንግስት ተቺዎቹን ካለበቂ ምክንያት በማሰር እና በመክሰስ እንዲሁም የኢንተርኔት አገልግሎትን በማቋረጥ ይተቻል። በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ መንግስት በተቃዋሚዎች ላይ የሚወስደው እርምጃ ያሳሰባቸው ዜጎች የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ጫና እንዲያሳድሩ የሚጠይቅ ፊርማ ማሰባሰብ ጀምረዋል። በዋይት ሐውስ አቤቱታ መቀበያ ገፅ ላይ የተጀመረው የፊርማ ማሰባሰብ እስካሁን ከ1500 በላይ ሰዎች የተካፈሉበት ሲሆን የባራክ ኦባማ መንግስት ጉዳዩን እንዲመለከተው 100,000 ሰዎች መፈረም ይኖርባቸዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በአማራ ክልል የተሰማራ ሲሆን በማህበራዊ ድረ-ገፆች በሚሰራጩ ያልተረጋገጡ መረጃዎች ተቃዋሚዎች መገደላቸው ተሰምቷል።