የኢትዮጵያ ምርጫና የመራጮች፣ የፖርቲዎችና የታዛቢዎች አስተያየት
እሑድ፣ ግንቦት 16 2007ኢትዮጵያ ዛሬ ያካሄደችዉ አምስተኛ አገር አቀፍ ምርጫ በሰላም መጠናቀቁ ተመልክቶአል። «ከማለዳ 12 ሰዓት ጀምሮ እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት ድረስ በመላ ሃገሪቱ የተካሄደዉ 5ኛው ሃገር አቀፍ ጠቅላላ ምርጫ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ በነፃነት ለሚፈልገው ፓርቲም ሆነ ዕጩ ድምፁን በመስጠት ላይ ይገኛል» ሲሉም የሃገሪቱ መገኛኛ ብዙኃኞች ዘግበዋል። እንድያም ሆኖ በተለያዩ የሃገሪቱ የምርጫ አካባቢዎች የሚገኙ ነዋሪዎች ምርጫዉ ጫና የበዛበት እንደነበረ ለዶይቼ ቬለ ሳይገልፁ አላለፉም።
በሰሜን ሸዋ ዞን ፤ ሸዋ ሮቢት ከተማ የሰማያሚ ፓርቲ የሶስት የምርጫ ጣቢያዎች ተዘዋዋሪ ታዛቢ አቶ ቴዎድሮስ ሀብቴ ሂደቱ ትንሽ ከበድ የሚል ነዉ ሲሉ ነዉ የተናገሩት።
«አንድ በኔ ስር ያለ ዜሮ ሁለት ጣብያ ላይ የሚገኝ ታዛቢ ይህ ምርጫ በኔ ግምት ሚዛናዊ አይደለም ፍትሃዊ አይደለም ብሎ ጥሎ ወጣ ። ከዚህ በኋላም አልታዘብም ስላለን እሱን የሚተካ ማስገባት ፈልገን ነበር። አንድ የገዥዉ ፓርቲ አባል የሆነ በጭራሽ እራሱ ነዉ የሚታዘባት ስላለ ሳይወድ በግዱ ስራዉን እንዲቀጥል ሆንዋል»
በሌላ በኩል ሆሳዕና በመሃል አራዳ አላባ ልዮ ወረዳ መራጭ ገነት ዳኘ በበኩላቸዉ ምርጫዉ ፍትሃዊ እንደነበረ ነዉ የገለፁት።
«በእኔ አስተያየት ምርጫዉ ነፃና ፍትሃዊ ነበር። ምርጫ ጣብያዉ በዲሞክራሲ መንገድ ገብተን በነፃነት ልማታችንን ያስቀጥለናል ብለን የምናምንበትን ፓርቲ መርጠን ነዉ የወጣነዉ። ፀጥታዉንም የሚያደፈርስ ነገር የለም በሰላም እየመረጥን ነዉ»
ምርጫዉ ሰላማዊ ቢሆንም በጎንደር ክልል አካባቢ የታደለዉ ባዶ የምርጫ ወረቀትነዉ ሲሉ አንድ የጎንደር ዩንቨርስቲ ተማሪ መልክት አድርሰዉናል።
«በዩንቨርስቲዉ ጊቢ ዉስጥ ነዉ እኔም የመረጥኩት። በርግጥ ምርጫዉ ሰላማዊ ነዉ። በምርጫዉ ጣብያ የጎንደር ክልል የአማራ ክልል የመቀሌ ተብሎ የተከፋፈለበት ሁኔታ አለ። ለምሳሌ የጎንደር ክልል ከገዥዉ ፓርቲ አርማ በስተቀር ባዶ የምርጫ ወረቀት የደረሳቸዉ እንዳሉ ታዉቋል።»
በወረዳችን አንድ ፓርቲ ብቻ ነዉ የተወዳደረዉ፤ ምርቻ መባሉ ለሥሙ ነዉ ያሉን የዶይቼ ቬለ ተከታታይ የባህር ዳር ዩንቨርስቲ ተማሪ በበኩላቸዉ፤ ምርጫዉ ሰላማዊ እንደነበር ግን ተናግረዋል።
ከሰሜን ወሎ አቶ ተመስገን ዘዉዱ በምርጫዉ ካርድ ላይ ምልክት ስናደርግ ተገደናል በዚህም ምክንያት መልዕክት ለናንተ ለማስተላለፍ ተገድጃለሁ ሲሉ አስተያየታቸዉን ሰጥተዋል።
በደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች ክልል በአላባ ልዩ ወረዳ የምርጫ አስተባባሪ አቶ ሞልቶት በበኩላቸዉ ምርጫዉ ከማለዳ ጀምሮ የሰመረ ነበር። ማጋነን ባይሆንብኝ በምርጫ ጣብያ ከለሊቱ አስራ አንድ ሰዓት ጀምሮ ሰዉ ዝግጁ ሆኖ ታይቷል ብለዋል። ሙሉ ዘገባዉን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ።
አዜብ ታደሰ
አርያም ተክሌ