የኢትዮጵያ ለዉጭ የቦንድ ሽያጭ ሃሳብ
ማክሰኞ፣ ጥቅምት 4 2007
መሆኑን ለሮይተርስ የተናገሩት ቃል አቀባዩ አቶ ሃጂ ኢብሳ ሌሎች የአፍሪካ ሃገሮች እንዳደረጉት ሁሉ ዩሮ ቦንድና ሌሎች የቦንድ አይነቶች ታሳቢ መደረጋቸውን ገልጸዋል።
ዓለም አቀፍ የቦንድ ገበያ መንግስታት በወጪና ገቢ ንግዶች መካከል የሚገጥማቸዉን ክፍተት ለመሸፈን ከሚጠቀሙባቸው መንገዶች አንዱ ነው። እስካሁን ኢትዮጵያ የመንግስት የግምጃ ቤት ሰነድን ሽያጭን የሚጠቀመዉ በሃገር ውስጥ ብቻ ነበር። አሁን ለዓለም አቀፍ የካፒታል ገበያ ለማቅረብ የታቀደዉ ቦንድ ግን ከቀደሞው የተለየ መሆኑን የኢኮኖሚ ባለሙያና የኢንቨስትመንት አማካሪ የሆኑት አቶ ጌታቸው ተክለማርያም ይናገራሉ።
''ሃገር ውስጥ ያለውን የመንግስት የግምጃ ቤት ሰነድ የሚመስለው ግን ደግሞ በአከፋፈል ሁኔታው ለውጭ ሃገር ኢንቨስተሮች የሚሆን መተማመኛ ሰነድ ነው።የምትሸጠው ቦንድ በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ውስጥ ገብቶ ሊተረጎም፤ሊሸጥ፤ተግባራዊ ሊሆን ሊሸጥ ሊቀየር የሚችል መሆን ይኖርበታል።ገበያው ውስጥ ሲገባ የሚገዙት እንደሚሸጥበት ሃገር ግለሰቦች፤የግል ተቋማት፤የፋይናንስ ተቋማት ና የጡረታ ፈንድ የሚያስተዳድሩ ድርጅቶች ሊሆኑ ይችላሉ።''
ይህ የቦንድ አለም አቀፍ ግብይት ከብሄራዊ ባንክ እና አለም አቀፍ አበዳሪዎች እንዲሁም ከእርዳታ በሚገኝ ገንዘብ ላይ ለተመሰረተው የኢትዮጵያ መንግስት ገቢ እፎይታ ነው የሚሉት አቶ ጌታቸው፤ የተጀመሩ ትልልቅ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ለማጠናቀቅም ያስችላታል ይላሉ።እንደ አቶ ጌታቸው ከሆነ የቦንድ ግብይቱ የሃገሪቱን ኢንቨስትመንትም ያበረታታል። ይሁንና በተነጻጻሪነት ከአለም ኢኮኖሚ ለየት ብሎ ለቆየው የኢትዮጵያ ገበያ ይህ የቦንድ ግብይት የሚያመጣቸው መልካም እድሎች የመኖራቸውን ያክል ፈተናዎችም እንዳሉት አቶ ጌታቸው ያስረዳሉ።
''የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ለሚያመጣው ተጽዕኖ መጀመሪያ ከነበረው የበለጠ ተጋላጭ ይሆናል።ሌላው ሃገሪቱ ቦንዱን ለገዙት ሰዎች ክፍያ በምትፈጽም ሰዓት በዶላር ወይም በዩሮ ነው ክፍያውን መፈጸም ያለባት።እንደ ኢትዮጵያ ላለ የውጭ ምንዛሪ ጫና ላለበት ሃገር ደግሞ እሱን ክፍያ መፈጸም ቀላል ነው ብለህ የምትገልጸው አይሆንም። ክፍያውን በምትፈጽምበት ሰዓት ክፍያውን ለመፈጸም የሚያስችል የውጭ ምንዛሬ ማፍራትና እሱን መመለስ የራሱ የሆነ ጫና ይኖረዋል።''
በአፍሪካ ካሁን ቀደም ኬንያ፤ ጋና፤ ናይጄሪያ፤ ጋቦን፤ ዛምቢያና ሴኔጋልን የመሳሰሉ ሃገራት ቦንድ በአለም አቀፍ ገበያ በመሸጥ ላይ ይገኛሉ። ሃገራቱ በአለም አቀፍ ገበያው ገዢዎች አላጡም የሚሉት አቶ ጌታቸው ኢትዮጵያን ጨምሮ ሁሉም ሃገራት የፋይናንስ ተቋሞቻቸው ውስን አቅም ግን ሁሉም የሚጋሩት ፈተና መሆኑን ይናገራሉ።
እሸቴ በቀለ
ነጋሽ መሃመድ